ቀጥታ, ኢራን ለተራዘመ ጦርነት መዘጋጀቷን ስትገልጽ፣ ትራምፕ ከጦር መሳሪያ አምራቾች ጋር ሊወያዩ ነው

ኢራን ከአሜሪካ ጋር ለድርድር መቀመጥ እንደማትፈልግ እና ለተራዘመ ጦርነት እየተዘጋጀች መሆኗን የሟቹ ጠቅላይ መሪ አሊ ኻሜኒ አማካሪ ተናገሩ። ፕሬዝዳንት ትራምፕ ደግሞ የአገራቸው የጦር መሳሪያ አምራቾች ምርታቸውን እንዲጨምሩ ለማዘዝ ስብሰባ ሲጠሩ፣ ተጨማሪ የመከላከያ በጀት ሊጠይቁ ነው።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ኢራን በባህሬን የሚገኝ የአሜሪካ አየር ኃይል ጦር ሰፈር ላይ ጉዳት ማድረሷን ገለፀች

    ኢራን በባህሬን በሚገኝ የአሜሪካ አየር ኃይል ጦር ሰፈር ላይ የፈጸመችው የሮኬት ጥቃት ጉዳት ማድረሱን ገለፀች።

    ፋርስ የተሰኘው የኢራን ዜና ወኪል ያጋራው ተንቀሳቃሽ ምስል ተከታታይ የሮኬት ጥቃቶች በርቀት የሚገኝ ዒላማ ላይ ሲወነጨፉ እና ሲፈነዱ ያሳያል።

    የኢራን አብዮታዊ ዘብ በባህሬን ሼክ ኢሳ ክልል በሚገኝ የአሜሪካ አየር ኃይል ማዘዣ እና ሠራተኞች ሕንጻ ላይ የፈጸማቸው የድሮን እና የሚሳዔል ጥቃቶች የነዳጅ ታንኮች ማፈንዳቱን ገልጿል።

    አሜሪካ በጉዳዩ ላይ እስካሁን የሰጠችው ምላሽ የለም።

    ቀደም ሲል በባህሬን ከሚገኝ የአሜሪካ ጦር ሰፈር ጭስ ሲወጣ ታይቶ ነበር።

    የአሜሪካ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አሜሪካውያን ከባህሬን እና ከሌሎች የመካከለኛው ምሥራቅ አገራት በፍጥነት ለቅቀው እንዲወጡ አስጠንቅቆ ነበር።

  2. ኢራን በሆርሙዝ ሰርጥ ላይ የሚንቀሳቀሱ መርከቦችን ለመምታት ዛተች

    በሆርሙዝ ሰርጥ እያለፈ ያለ የነዳጅ ጫኝ መርከብ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ቴህራን እስራኤል እና አሜሪካ የከፈቱትን ጥቃት ተከትሎ በዓለም ወሳኙ የነዳጅ ዘይት መተላለፊያ በሆነው የሆሙዝ የባሕር ሰርጥን ላይ ለማለፍ በሚሞክሩ መርከቦች ላይ ጥቃት እንደምትፈጽም ዛተች።

    አንድ ኢራን ባለሥልጣን በሆሙዝ ሰርጥ “ለማለፍ የሚሞክር ማንኛውም መርከብን በእሳት ነው የምንለኩሰው” ሲሉ አስጠንቅቀዋል።

    ማስጠንቀቂያውን የሰጡት ባለሥልጣን የኢራን እስላማዊ አብዮት ዘብ ዋና አዛዥ አማካሪ የሆኑት ኢብራሂም ጃባሪ በአገሪቱ ብሔራዊ ቴሌቪዥን ቀርበው በተናገሩበት ወቅት ነው።

    የሆርሙዝ ሰርጥ መዘጋቱን ያስጠነቀቁት ባለሥልጣኑ መርከቦች “ወደ ቀጠናው መምጣት የለባቸውም። ከባድ የሆነ ምላሽ ከእኛ ይጠብቃቸዋል” ሲሉ ዝተዋል።

    ጃባሪ አሜሪካ “የቀጠናውን የነዳጅ ዘይት ተጠምተዋል” ያሉ ሲሆን ኢራን “በቀጠናው የሚገኙ የነዳጅ ማስተላለፊያ ቧንቧዎችን ታጠቃለች፤ ከቀጠናው ነዳጅ እንዲላክ አትፈቅድም” ብለዋል።ኢራን የሆርሙዝ ሰርጥን ብትዘጋ በቀሪው ዓለም ላይ ምን ሊከሰት ይችላል?

  3. ሩቢዮ አሜሪካ ኢራን ላይ “ቀድማ” ጥቃት የሰነዘረችው እስራኤል ጥቃት እንደምትሰነዝር እያወቀች መሆኑን ተናገሩ

    ማርኮ ሩቢዮ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማርኮ ሩቢዮ አሜሪካ ቅዳሜ ዕለት ኢራንን "አስቀድማ” ያጠቃችው እስራኤል ጥቃት ልትሰነዝር እንደሆነ ስለተገነዘቡ መሆኑን ተናገሩ።

    ይህም ኢራን በአሜሪካ ኃይሎች ላይ የበቀል እርምጃ እንድትወስድ ያደርጋታል ብለዋል።

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ከዚህ ቀደም ብለው ለጋዜጠኞች "እስራኤል እርምጃ እንደምትወሰድ እናውቅ ነበር። ይህም በአሜሪካ ኃይሎች ላይ ጥቃት እንዲሰነዘር እንደሚያደርግ እናውቃለን።"

    ሩቢዮ አክለውም "እናም እነዚያን ጥቃቶች ከመጀመራቸው በፊት ቀድመን ካላጠቃን፣ ከፍተኛ ጉዳት እንደሚደርስብን እና ምናልባትም የሚሞቱ ሰዎች ቁጥር ከፍ ያለ እንደሚሆን እናውቅ ነበር" ብለዋል።

    “የታክቲካል ጥረታችንን ዝርዝር መረጃ አልሰጥም፤ ነገር ግን አሜሪካ ኢራን ላይ የምትፈጽማቸው በጣም ከባድ ጥቃቶች ገና ናቸው” ሲሉ አክለዋል።

  4. አሜሪካ ኢራን ላይ “መጠነ ሰፊ ወታደራዊ እርምጃ” መውሰድ እንደምትቀጥል ትራምፕ ተናገሩ

    ዶናልድ ትራምፕ

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ “በኢራን ላይ የሚወሰደው መጠነ ሰፊ ወታደራዊ እርምጃ” እንደሚቀጥል አስታወቁ።

    የኢራን መንግሥት የኒውክሌር የጦር መሣሪያ ግንባታ እንዲያቆም ከአሜሪካ የተሰጠውን ማስጠንቀቂያ ችላ እንዳለም ገልጸዋል። ከቴህራን የተደቀነውን አደጋ ለመቀልበስ እርምጃ መውሰድ እንደሚቀጥሉም ተናግረዋል።

    ለአሜሪካ ወታደሮች ሜዳልያ ለመስጠት በተዘጋጀ ሥነ ሥርዓት ላይ ንግግር ያደረጉት ትራምፕ “የኢራን የሚሳዔል መርሃ ግብር የኒውክሌር ግንባታን ለመሸፈን ያለመ ነበር” ሲሉም ተደምጠዋል።

    ኒውክሌር የጦር መሣሪያ እና የረዥም ርቀት ሚሳዔል የታጠቀ የኢራን መንግሥት መካከለኛው ምሥራቅ እና የአሜሪካ ሕዝብ “ሊታገሱት የማይገባ ስጋት ነው” ብለዋል።

    በኢራን ላይ እየወሰዱ ያሉት እርምጃ አላማው የአገሪቱን “የሚሳዔል ግንባታ አቅም እንዲሁም የባሕር ኃይል ማምከን” መሆኑን ፕሬዝዳንቱ ገልጸዋል።

    “በተገደሉት የአሜሪካ ወታደሮች ስም ዘመቻውን አጠናክረን እንቀጥላለን” ብለዋል።

    በኢራን ላይ እየተካሄደ ያለው ዘመቻ አሜሪካ ከያዘችው የጊዜ ሰሌዳ “በጣም እንደቀደመ” ፕሬዝዳንቱ ገልጸዋል።

    ዘመቻው ከመነሻው ላይ ከአራት እስከ አምስት ሳምንት እንደሚወስድ እንደተገመተ የጠቀሱት ትራምፕ “ከዚያም በላይ የመዝለቅ አቅም አለው” ሲሉ ተናግረዋል።

  5. ኢራን በኳታር እና በሳዑዲ የነዳጅ ማዕከላት ላይ የፈጸመችውን ጥቃት ተከትሎ ከፍተኛ የዋጋ ጭማሪ ታየ

    ጭስ የሚታይበት የነዳጅ ማጣሪያ እና የሥራ ሄልሜት ያደረገ ሠራተኛ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ከሳዑዲ ነዳጅ ማጣሪያ ሠራተኞች ለቀው እንዲወጡ ተደርገዋል

    ኢራን በኳታር እና በሳዑዲ አረቢያ የነዳጅ ማምረቻ ተቋማት የሰነዘረቻቸው ጥቃቶች በምርት ላይ ተጽዕኖ ይኖራቸዋል በሚል ስጋት በአውሮፓ ውስጥ ከፍተኛ የዋጋ ጭማሪ መታየቱ ተዘገበ።

    የኳታር መንግሥት ንብረት በሆነው የኤልፒጂ ጋዝ ማምረቻ ‘ኳታርኢነርጂ’ የተወሰኑ ክፍሎቹ ላይ ኢራን በሰነዘረችው ጥቃት ሳቢያ ምርት መቆሙን አስታውቋል።

    የባሕረ ሰላጤዋ አገር ኳታር በተፈጥሮ ጋዝ ምርቷ በዓለም ላይ ቀዳሚ ከሆኑት ከአሜሪካ፣ ከአውስትራሊያ እና ከሩሲያ ጋር የምትጠቀስ አገር ናት።

    በኳታር የጋዝ ማረምቻ ላይ ጥቃት መፈጸሙ ከተሰማ ከአጭር ጊዜ በኋላ በአውሮፓ ውስጥ የተፈጥሮ ጋዝ ዋጋ ላይ 50 በመቶ ጭማሪ ታይቷል።

    በተመሳሳይ የሳዑዲ አረቢያ መከከላያ ሚኒስቴርን ጠቅሶ የአገሪቱ ዜና ወኪል እንደዘገበው ዛሬ ሰኞ ጠዋት ሁለት ድሮኖች ራስ ታኑራ በተባለው የነዳጅ ማጣሪያ ላይ “ጥቃት ለመፈጸም ሙከራ” አድርገዋል። ድሮኖቹን ለማክሸፍ በተደረገው ሙከራ “ትንሽ” እሳት መነሳቱም ተነግሯል።

    ጥቃት የተሰነዘረበት ነዳጅ ማጣሪያ በዓለም ትልቅ ከሆኑት ማጣሪያዎች መካከል አንዱ ሲሆን በቀን 550 ሺህ በርሜል ነዳጅ የማጣራት አቅም አለው።

    ይህ የነዳጅ ማጣሪያ በመካከለኛው ምሥራቅ ውስጥ ካሉት ትልቁ ሲሆን፣ ለሳዑዲ አረቢያ ነዳጅ ምርት ተቀዳሚው ተጠቃሽ ማዕከል ነው።

    ይህ በኳታር እና በሳዑዲ የነዳጅ ማምረቻ ተቋማት ላይ ጥቃት የተሰነዘረው መርከቦች የዓለም አንድ አምስተኛው ነዳጅ እና አብዛኛው የኳታር የተፈጥሮ ጋዝ በሚተላለፍበት የሆርሙዝ ሰርጥ ጥቃት ይፈጸማል በማለት መርከቦች በቆሙበት ጊዜ ነው።

    የባሕር ላይ እንቅስቃሴ መስተጓጎል፣ በነዳጅ ተቋማት ላይ የሚፈጸመው ጥቃት እና ጦርነቱ ሊራዘም ይችላል የሚለው ስጋት በዓለም የነዳጅ ዋጋ ላይ ከፍተኛ ጭማሪ አስከትሏል።

  6. የአያቶላህ አሊ ኻሜኒ ሚስት መገደላቻውን የኢራን ቴሌቪዥን አረጋገጠ

    በኻሜኒ ሞት ያዘኑ ኢራናውያን ሴቶች ፎቷቸውን ይዘው

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, በኻሜኒ ሞት ያዘኑ ኢራናውያን ሴቶች ፎቷቸውን ይዘው

    አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ በፈጸሙት ጥቃት የተገደሉት የኢራን ጠቅላይ መሪ አያቶላህ አሊ ኻሜኒ ሚስት መገደላቸውን የአገሪቱ መንግሥት ቴሌቪዥን አረጋገጠ።

    የጠቅላይ መሪው ሚስት ማንሱሬህ ኾጃስቴ ባግሄርዛዴህ የተገደሉት “ቤታቸው ውስጥ” መሆኑን ቴሌቪዥን ጣቢያው ገልጿል። ቀደም ሲል የኢራን መገናኛ ብዙኃን ግለሰቧ “ኮማ” ውስጥ እንደነበሩ ዘግበው ነበር።

    ቅዳሜ ዕለት በተፈጸመው ጥቃት ከአያቶላህ ኻሜኒ በተጨማሪ ሴት ልጃቸው፣ የልጃቸው ባል እና የልጃቸው ልጅ መገደላቸው ተዘግቧል።

    የጠቅላይ መሪው ሚስት ከአያቶላህ ኻሜኒ አራት ወንዶች እና ሁለት ሴት ልጆች ነበሯቸው።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ የእስራኤል ጦር እሑድ በሊባኖስ፣ ቤይሩት ውስጥ በፈጸመው ጥቃት የሔዝቦላህን የደኅንነት ኃላፊ መግደሉን አስታውቋል።

    የእስራኤል ጦር ኃይል “እሑድ ምሽት ቤይሩት ውስጥ በተፈጸመ የተነጣጠረ ጥቃት፣ የሔዝቦላህ የደኅንነት ተቋም አዛዥ የሆነውን ሽብርተኛው ሑሴን ማክሌድን መደምሰሱን አረጋግጧል” ሲል ባወጣው መግለጫ ላይ አስፍሯል።

  7. ከዱባይ የሚወጡ የተወሰኑ ሰዎችን የያዙ በረራዎች ሊደረጉ ነው

    የዱባይ አውሮፕላን ማረፊያ “የተወሰኑ በረራዎችን” ዛሬ ምሽት ላይ እንደሚጀምር አስታወቀ።

    በረራዎቹ ከዓለም አቀፉ የዱባይ አውሮፕላን ማረፊያ እና ከአል ማክቱም ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ የሚነሱ ይሆናል።

    ሆኖም ግን ከአየር መንገድ ጥሪ ያልደረሳቸው ተጓዦች ወደ አውሮፕላን ማረፊያ እንዳይሄዱ አሳስቧል።

    ዱባይ የሚገኘው ኤምሬትስ አየር መንገድ “ቀድመው ለበረራ የተመዘገቡ ተጓዦችን” እንደሚያስተናግድ አስታውቋል።

    በሌላ በኩል ጀርመን በመካከለኛው ምሥራቅ የሚገኙ ዜጎቿ የሆኑ ቱሪስቶችን ለማስወጣት አውሮፕላኖች እንደምትልክ ተገልጿል።

    የዩናይትድ ኪንግደም መንግሥትም ዜጎቹን ለማስወጣት እየሠራ እንደሆነ የገለጸ ሲሆን፤ 100 ሺህ ሰዎች መመዝገባቸውን አስታውቋል።

  8. “አሜሪካ በኢራን ላይ የወሰደችውን እርምጃ እንደግፋለን”- ኔቶ

    የሰሜን አትላንቲክ ጦር ቃልኪዳን (ኔቶ) ዋና ጸሐፊ ማርክ ሩቴ
    የምስሉ መግለጫ, የሰሜን አትላንቲክ ጦር ቃልኪዳን (ኔቶ) ዋና ጸሐፊ ማርክ ሩቴ

    የሰሜን አትላንቲክ ጦር ቃል ኪዳን ማኅበር (ኔቶ) ዋና ጸሐፊ ማርክ ሩተ፤ አሜሪካ በኢራን ላይ የወሰደችውን እርምጃ “እንደግፋለን” ሲሉ ለቢቢሲ ተናገሩ።

    ኢራን ለአውሮፓ፣ ለእስራኤል እንዲሁም ለቀጣናው “ስጋት ናት” ያሉት ማርክ ሩተ፤ በቴህራን ላይ ከሚወሰደው እርምጃ ጋር በተያያዘ “አውሮፓ እየተጠናከረ ነው” ብለዋል።

    አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ ጥቃት ለመፈጸም እየተዘጋጁ እንደነበር ቀድመው ያውቁ እንደሆነ ከቢቢሲ የተጠየቁት ዋና ጸሐፊው ዝርዝር ጉዳዮችን በይፋ መናገር እንደማይሹ ገልጸዋል።

    ሩተ ከአሜሪካ ባለሥልጣናት ጋር “ብዙ ንግግር” ማድረጋቸውን ጠቅሰው፤ ዋሽንግተን እና ኔቶ “በቅርበት እየተጋገዙ ነው” ብለዋል።

    ኔቶ በኢራን ላይ የሚወሰደውን እርምጃ የሚቀላቀል እንደሆነ ተጠይቀው “በፍጹም፤ ይሄ በግልጽ የአሜሪካውያን እና የእስራኤላውያን ዘመቻ ነው” ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል።

    “ኔቶ እና በቀጣናው ያሉ ወዳጆቻችን በኢራን ጥቃት ተከፍቶባቸዋል። በዚህ ሁኔታ ውስጥ ማድረግ የሚችሉትን እያደረጉ ነው” በማለትም ለቢቢሲ ተናግረዋል።

  9. “ጦርነቱን አልጀመርነውም፤ ግን እንጨርሰዋለን”- የአሜሪካ መከላከያ ጸሐፊ

    የአሜሪካ መከላከያ ጸሐፊ ፒት ሄግዚት
    የምስሉ መግለጫ, የአሜሪካ መከላከያ ጸሐፊ ፒት ሄግዚት

    የአሜሪካ መከላከያ ጸሐፊ ፒት ሄግዚት፤ በኢራን ላይ የሚወሰደው እርምጃ “በታሪክ በጣም የከፋው፣ ውስብስብ የሆነ እና ዒላማውን የመታ” እንደሆነ ተናገሩ።

    የመከላከያ ጸሐፊው ዛሬ በሰጡት መግለጫ “ጦርነቱን እኛ አልጀመርነውም ግን በፕሬዝዳንት ትራምፕ አስተዳደር ሥር እንጨርሰዋለን” ብለዋል።

    ኢራን የኒውክሌር ጦር ለመገንባት አይደለም በሚል “እየዋሸችን ነበር” ያሉት ፒት ሄግዚት” አሜሪካ በኢራን ላይ የምታደርሰው ጥቃት “ወደማያልቅ ጦርነት” እንደማያመራም ገልጸዋል።

    የአሜሪካ ግብ የቴህራንን ሚሳዔል እና የደኅንነት መዋቅር መበጣጠስ እንደሆነ ተናግረዋል።

    ኢራን የኒውክሌር መርሃ ግብሯ ሰላማዊ እንደሆነ በተደጋጋሚ ብትገልጽም የመከላከያ ጸሐፊው ግን “ሰላማዊ የኒውክሌር ፍላጎት ተራራ ሥር አይደበቅም” ብለዋል።

    ቴህራን “በሰላማዊ መንገድ እና በምክንያታዊነት” ከአሜሪካ ጋር ለመደራደር እንዳልፈቀደችም ተናግረዋል።

    “ሚሳዔል ለማከማቸት እና የኒውክሌር ጦር ግንባታ ፍላጎታቸውን ለማሳካት ጊዜ እየገዙ ነበር። ፕሬዝዳንት ትራምፕ እንዲህ ያለ ጨዋታ አይፈልጉም” ሲሉም በመግለጫቸው አክለዋል።

    ኢራናውያን ይሄንን "ታላቅ ዕድል" ሊጠቀሙበት ይገባል ሲሉም ተደምጠዋል።

  10. በመካከለኛው ምሥራቅ ውጥረት ምክንያት ዓለም አቀፍ የነዳጅ ዋጋ ጨመረ

    በመካከለኛው ምሥራቅ በግጭት እየተናጠ ባለበት በአሁኑ ወቅት ዓለም አቀፍ የነዳጅ ዋጋ እየናረ ይገኛል።

    የኳታር የተጣራ ጋዝ ማምረቻ በኢራን ጥቃት ከተፈጸመበት በኋላ ምርት ማቋረጡን አገሪቱ አስታውቃለች። ‘ኳታርኢነርጂ’ የተባለው የኳታር መንግሥት የሚያስተዳድረው የነዳጅ አምራች በኢራን ጥቃት ተፈጽሞበታል።

    ኳታር ዋነኛ የተጣራ ጋዝ አምራች አገር ስትሆን፤ ከዓለም ገበያ አንድ አምስተኛውን ትቆጣጠራለች።

    ኳታር የተጣራ ጋዝ ወደ ውጭ አገራት የምትልከው በሆርሙስ ሰርጥ በኩል ሲሆን፤ በዋናነት በደቡብ እና ምሥራቅ እስያ ታከፋፍላለች።

    በኳታር የነዳጅ አቅርቦት ላይ የሚፈጠር መስተጓጎል ዓለም አቀፍ ገበያ ላይ ጫና ያሳድራል። በእስራኤል የሚገኙ የተወሰኑ የነዳጅ ተቋማትም ሥራ ማቋረጣቸው ችግሩን አባብሷል።

    ተንታኞች እንደሚሉት ይህ መስተጓጎል በአውሮፓ ገበያ ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ የሚያሳድር ይሆናል።

  11. የሊባኖስ መንግሥት የሄዝቦላህን ወታደራዊ እንቅስቃሴ አገደ

    ሄዝቦላህ ዛሬ ጠዋት ወደ እስራኤል ሮኬት ሲተኩስ ነበር።

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ሄዝቦላህ ዛሬ ጠዋት ወደ እስራኤል ሮኬት ሲተኩስ ነበር።

    የሊባኖስ መንግሥት በመላው አገሪቱ የሄዝቦላህን ወታደራዊ እንቅስቃሴ ማገዱን አስታወቀ። ሄዝቦላህ ዛሬ ጠዋት ወደ እስራኤል ሮኬት ሲተኩስ ነበር።

    ሄዝቦላህ ሮኬቶች ሲተኩስ ከሊባኖስ መንግሥት ጋር እንዳልተነጋገረ ተገልጿል። የሊባኖስ መንግሥት ውሳኔ ከሄዝቦላህ ጋር አጣብቂኝ ውስጥ የሚከተው እንደሆነ ይታመናል።

    የሊባኖስ መንግሥት በቀጣናዊ ውጥረት ውስጥ እጁን ማስገባት ባይፈልግም ሄዝቦላህ ግን እስራኤል ላይ ሮኬቶች ተኩሷል።

    የሊባኖስ ፕሬዝዳንት ጆሴፍ አውን እና ጠቅላይ ሚኒስትር ኑዋፍ ሳላም ጥቃቱ የአገሪቱን ሉዓላዊነት ይጥሳል ብለዋል። እስራኤል የአጸፋ እርምጃ እንድትወስድ በማነሳሳት ሊባኖስን ወደ ቀጣናዊው ግጭት እንደሚያስገባም አስጠንቅቀዋል።

  12. አሜሪካ ተዋጊ አውሮፕላኖቿ በኩዌት የወደቁት ጥቃት ደርሶባቸው እንዳልሆነ ገለጸች

    አሜሪካ ተዋጊ አውሮፕላኖቿ በኩዌት የወደቁት ኢራን ላይ የተከፈተውን ጥቃት ሲያከናውኑ በተፈጠረ ድንገተኛ ክስተት እንጂ ጥቃት ደርሶባቸው እንዳልሆነ አስታወቀች።

    የኩዌት የመከላከያ ሚኒስቴር "ዛሬ ጠዋት በርካታ የአሜሪካ ተዋጊ አውሮፕላኖች ተከስክሰዋል" ማለቱ ይታወሳል።

    የመከላከያ ሚኒስቴሩ አክሎም ከአሜሪካ ጋር ስለ "ክስተቱ" እየተነጋገረ እንደሆነ እና "የክስተቱን መንስዔዎች" በተመለከተ ምርመራ እየተካሄደ እንደሆነ አስታውቋል።

    የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ፤ ኤፍ-15 ተዋጊ ጀቶቹ ‘ኢፒክ ፊውሪ’ የሚል ስያሜ የተሰጠውን እና ኢራን ላይ የሚፈጸመውን ጥቃት እያከናወኑ ሳለ በኩዌት መውደቃቸውን አስታውቋል።

    ስድስት የበረራ አባላት ጉዳት ሳይደርስባቸው ከአውሮፕላኖኑ እንዲወጡ መደረጉንም አክሏል።

    የኩዌት መከላከያ ሚኒስቴርም የበረራ አባላቱ ሁኔታ "የተረጋጋ" መሆኑን ገልጾ ነበር።

  13. ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ በኩዌት ሉዓላዊ ግዛት ላይ የተፈጸመውን ጥቃት አወገዙ

    ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ እና የኩዌት ልዑል አልጋ ወራሽ ሼክ ሳባህ ኻሊድ አል ሀማድ አል ሳባህ

    የፎቶው ባለመብት, BBC/KUNA

    የምስሉ መግለጫ, ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ እና የኩዌት ልዑል አልጋ ወራሽ ሼክ ሳባህ ኻሊድ አል ሀማድ አል ሳባህ በስልክ መወያየታቸው የተገለጸው ትናንት እሁድ ዕለት ነው

    ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ እሁድ ዕለት ኢራን በኩዌት ላይ የፈጸመችውን ጥቃት ተከትሎ ከኩዌት ልዑል አልጋ ወራሽ ሼክ ሳባህ ኻሊድ አል ሀማድ አል ሳባህ ጋር በስልክ መወያየታቸው ተገለፀ።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ከኩዌቱ ልዑል አልጋ ወራሽ ጋር ባደረጉት ውይይት በአገሪቱ ሉዓላዊ ግዛት እና የአየር ክልል ላይ የሚፈጸም ጥቃትን በጽኑ ማውገዛቸውን የኩዌት የዜና ወኪል ዘግቧል።

    ዐቢይ፤ ድርጊቱ የዓለም አቀፍ ሕግ እና የተባበሩት መንግሥታት ቻርተር ጥሰት ነው ማለታቸውን ዘገባው ያመለክታል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ከልዑል አልጋ ወራሹ ጋር በነበራቸው የስልክ ንግግር ወቅት የኩዌት ዜጎች እና ተቋማት ላይ የሚደርሱ ጥቃቶችን ማውገዛቸው ተገልጿል።

    ዘገባው እንደሚያመለክተው ዐቢይ፤ በኩዌት የሲቪል ተቋማት ላይ የሚፈጸም ጥቃት ተቀባይነት እንደሌለውም ተናግረዋል።

    ዐቢይ ኢትዮጵያ፣ የኩዌት መንግሥት እና አመራር የአገሪቱን ሉዓላዊነት፣ መረጋጋት እና ደኅንነት ለመጠበቅ በሚወስደው ማንኛውም እርምጃ ድጋፋቸውን ገልጸዋል።

    ኢራን በትናንትናው ዕለት በመካከለኛው ምሥራቅ በፈጸመችው ጥቃት በኩዌት የአንድ ሰው ሕይወት ማለፉ ተገልጿል።

    ኢራን በበርካታ የመካከለኛው ምሥራቅ አገራት ላይ ዛሬም ጥቃት የፈጸመች ሲሆን በባህሬን፣ ዱባይ እንዲሁም በኩዌት የአሜሪካ ኤምባሲ አቅራቢያ ፍንዳታዎች መሰማታቸውን የአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    የኩዌት ልዑል አልጋ ወራሽ ሼክ ሳባህ ኻሊድ አል ሀማድ አል ሳባህ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይን ስላሳዩት ድጋፍ እንዳመሰገኑም የዜና ወኪሉ ዘግቧል። የዓለም መንግሥታት በኢራን ላይ ስለደረሰው ጥቃት ምን አሉ?

  14. ትራምፕ አያቶላህ አሊ ኻሜኒን ሊተኩ የሚችሉ በርካታ ዕጩዎች በመጀመሪያው ዙር ጥቃት ተገድለዋል አሉ

    ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, reu

    ዶናልድ ትራምፕ ከአሜሪካው የቴሌቪዥን ጣቢያ ኤቢሲ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ አያቶላህ አሊ ኻሜኒን ይተካሉ ተብለው ተስፋ የሚጣልባቸው አብዛኞቹ ዕጩዎች በመጀመርያው ዙር ጥቃት ተገድለዋል አሉ።

    የኤቢሲ ጋዜጠኛ የሆነው ጆናታን ካርል በማኅበራዊ ሚዲያ ገፁ ላይ ከአሜሪካው ፕሬዚዳንት ጋር በስልክ በነበረው ቃለ ምልልስ ላይ “አብዛኞቹን እጩዎች በማስወገድ ረገድ ውጤታማ ነበርን” እንዳሉት ጽፏል።

    የኢራን ጠቅላይ መሪ አያቶላህ አሊ ኻሜኒ በአሜሪካ እና በእስራኤል የአየር ጥቃት ቅዳሜ የካቲት 21/2018 ዓ.ም. ተገድለዋል።

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከዚህ ቀደም ኢራንን ለመምራት ሦስት ጥሩ አማራጮች መኖራቸውን ተናግረው የነበሩ ቢሆንም ስማቸውን ከመዘርዘር ግን ተቆጥበዋል።

    እሁድ ዕለት የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ በኢራን በተፈጸመ ጥቃት ሦስት አሜሪካ ወታደሮች መገደላቸውን እና አምስት ደግሞ የመቁሰል አደጋ እንደደረሰባቸው ካረጋገጠ በኋላ "ተጨማሪ" አሜሪካውያን ላይ ጉዳት ሊደርስ እንደሚችል ፕሬዝዳንት ትራምፕ ተናግረዋል።

  15. ሳይፕረስ ውስጥ የሚገኝ የብሪታኒያ የጦር ሰፈር በኢራን ድሮን ተመታ

    የዩናይትድ ኪንግደም የጦር ሰፈር መግቢያ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ሳይፕረስ ውስጥ የሚገኘው የጦር ሰፈር የብሪታኒያ ሊዓላዊ ግዛት ነው

    ትናንት ምሽት ሳይፕረስ ውስጥ በሚገኘው የዩናይትድ ኪንግደም የጦር ሰፈር ላይ የድሮን የጥቃት መፈጸሙን የብሪታኒያ መከላከያ ሚኒስቴር ገልጿል።

    በኢራን ድሮን ጥቃት የደረሰበት ‘አርኤኤፍ’ የተባለው የጦር ሰፈር በሳይፕረስ የሚገኝ የብሪታኒያ ሉዓላዊ ግዛት ነው።

    የሳይፕረስ ፕሬዝዳንት ኒኮስ ክርስቶዶውሊደስ፤ በደቡባዊ አገሪቱ ክፍል በሚገኘው የዩናይትድ ኪንግደም የጦር ሰፈር ላይ የደረሰውን የድሮን ጥቃት በተመለከተ ተጨማሪ መረጃዎች ሰጥተዋል።

    እኩለ ሌሊት እንዳለፈ፤ “ሻሄድ ሰው አልባ በራሪ” አክሮቲሪ ውስጥ ከሚገኙ የዩናይትድ ኪንግደም ወታደራዊ ተቋማት ላይ መውደቁን ተናግረዋል። ፕሬዝዳንቱ የጠቀሱት ሻሄድ የኢራን ድሮኖች ናቸው።

    በዚህ ጥቃት “መጠነኛ ቁሳዊ ጉዳት” እንደደረሰ ፕሬዝዳንቱ በኤክስ ገጻቸው አስታውቀዋል። ከአውሮፓውያን እና ሌሎች መሪዎች ጋር “በቋሚነት ግንኙነት” እያደረጉ እንደሆነ ገልጸዋል።

    አክለውም ግን ሳይፕረስ “ምንም ዓይነት ወታደራዊ ዘመቻ ውስጥ የመሳተፍ ዕቅድ እንደሌላት” ተናግረዋል።

    የብሪታኒያ መከላከያ ሚኒስቴር በበኩሉ “የሠራተኞቻችን እና የቤተሰቦቻቸው ደኅንነት ፍጹም ቅድሚያ የሚሰጠው ጉዳይ ነው” ብሏል።

    ለጥንቃቄ እርምጃ ሲባልም በጦር ሰፈሩ የሚገኙ የቤተሰብ አባላት ወደ “ከሳይፕረስ ደሴት አቅራቢያ ወደሚገኝ” ስፍራ መዘዋወራቸውን አስታውቋል።

    ዛሬ ጠዋት ላይ ፖሊስ ወደ ጦር ሰፈሩ የሚወስድ መንገድ ላይ ፍተሻ ሲያደርግ ታይቷል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

  16. እስራኤል በሊባኖስ በፈጸመችው ድብደባ 31 ሰዎች ተገደሉ

    ኢያል ዛሚር (በስተቀኝ) ከጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ ጋር

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የምስሉ መግለጫ, ኢያል ዛሚር (በስተቀኝ) ከጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ ጋር

    እስራኤል በደቡባዊ ሊባኖስ በፈጸመችው ጥቃት 31 ሰዎች ሲገደሉ 149 ደግሞ ጉዳት እንደ ደረሰባቸው የአገሪቱ ጤና ሚኒስቴር አስታወቀ።

    የእስራኤል መከላከያ በሄዝቦላህ ላይ “የማጥቃት ዘመቻ” መክፈቱን የገለፀ ሲሆን ይህም ለበርካታ ቀናት ሊቆይ ይችላል ብሏል።

    የእስራኤል መከላከያ አዛዡ ኢያል ዛሚር "በሄዝቦላህ ላይ የማጥቃት ዘመቻ መጀመራችን ነው። በመከላከል ላይ አይደለም ያለነው፤ እያጠቃን ነው” ብለዋል።

    አክለውም “ለበርካታ ቀናት ለሚቀጥል ውጊያ መዘጋጀት አለብን፤ ለብዙ ቀናት። ጠንካራ የመከላከል ዝግጁነት ያስፈልገናል። እንዲሁም ቀጣይነት ላለው ማጥቃት ዝግጁ መሆን አለበን” ብለዋል።

    ኢራን በበርካታ የመካከለኛው ምሥራቅ አገራት ላይ የምትፈጽመውን ጥቃት ዛሬም ቀጥላለች። በባህሬን እና ዱባይ እንዲሁም በኩዌት የአሜሪካ ኤምባሲ አቅራቢያ ፍንዳታዎች መሰማታቸውን የአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    የእስራኤል ጦር ቃል አቀባይ ሠራዊቱ ከሔዝቦላህ ጋር ዳግም ውጊያ መግጠሙን ተከትሎ ወደ ሊባኖስ የእግርኛ ሠራዊት ይሰማራ እንደሆን ተጠይቀው "ሁሉም አማራጮች ጠረጴዛ ላይ ናቸው" ሲሉ መልሰዋል።

    ሔዝቦላህ እስራኤልን ላይ ጥቃት በመሰንዘሩ "ከባድ ዋጋ ይከፍላል" ሲሉ ተናግረው “ዝግጁ ነን፤በሚገባ ተዘጋጅተናል። ወደ 100,000 የሚጠጉ ተጠባባቂ ወታደሮችን አሰባስበናል፤ በደርዘን የሚቆጠሩ ሻለቃዎችን፣ ብርጌዶችን፣ ዕዞችን፣ የሰሜን ድንበርን ለመከላከል አሰማርተናል፣ እና ለመከላከልም ሆነ ለማጥቃት ለሚደረጉ ሁሉም አማራጮች ተዘጋጅተናል" ብለዋል።

    "የሁኔታ ግምገማዎችን እያካሄድን ነው፣ እና ሁሉም አማራጮች በጠረጴዛ ላይ ናቸው።"

  17. ኢራን በኩዌት እና ኢራቅ ላይ ጥቃት መፈጸሟ ተገለጸ

    ኢራን በኩዌት የፈጸመችውን ጥቃትን ተከትሎ ጭስ ታይቷል

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ኢራን በኩዌት የፈጸመችውን ጥቃትን ተከትሎ በከተማዋ ጭስ ታይቷል

    አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ የሚፈጽሙትን ጥቃት ለሦስተኛ ቀን በቀጠሉበት በዛሬው ዕለት ኢራንም በባሕረ ሰላጤው አካባቢ ባሉ አገራት ላይ ሚሳዔሎችን አስወንጭፋለች።

    ዛሬ ማለዳ በኩዌት የሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ አቅራቢያ ጥቃት መፈጸሙ ተገልጿል።

    ኤምባሲው በኩዌት የሚገኙ የአሜሪካ ዜጎች ወደ ኤምባሲው እንዳይመጡ እና በቤታቸው እንዲቆዩ መልዕክት አስተላልፏል።

    በኤምባሲው ድረገጽ ላይ የሰፈረው መልዕክት “ወደ ኤምባሲው እንዳትመጡ” ካለ በኋላ ቤታቸው ውስጥ ደህንነቱ በተጠበቀ ሥፍራ እንዲሆኑ መመሪያ አስተላልፏል።

    አክሎም “መስኮት አካባቢ አትቅረቡ፤ ወደ ውጭ አትውጡ” ሲል በአገሪቱ ለሚኖሩ አሜሪካውያን የደህንነት መልዕክቶችን አስፍሯል።

    ኢራን በመካከለኛው ምሥራቅ ትናንት በፈጸመችው ጥቃት በኩዌት አንድ ሰው መገደሉ ተገልጿል። የአሜሪካ አጋር የሆነችው ኩዌት ከኢራን የተተኮሰባትን ሚሳዔል ማክሸፏን አስታውቃለች።

    ሮይተርስ የዜና ወኪል በበኩሉ በኢራቅ የሚገኙ የደኅንነት ባለሥልጣናትን በመጥቀስ በሰሜናዊ የአገሪቱ ክፍል በሚገኘው በኢርቢል አውሮፕላን ማረፊያ ሦስት የታጠቁ ሰው አልባ አውሮፕላኖችን መትቶ መጣሉን አስታውቋል።

    በአውሮፕላን ማረፊያው የአሜሪካ ወታደሮች ይገኛሉ ተብሏል።

    ሮይተርስ ሰው አልባ አውሮፕላኖቹ ተመትተው መውደቃቸውን የገለፀው በጦር ሠፈሩ ከፍተኛ ፍንዳታ መሰማቱን የኤኤፍፒ ጋዜጠኛ ከዘገበ በኋላ ነው።

    በሳምንቱ መጨረሻ አሜሪካ ሰው አልባ አውሮፕላኖችን ማክሸፏን አስታውቃለች።

  18. ሰበር, የአሜሪካ ወታደራዊ አውሮፕላኖች በኩዌት ተከሰከሱ

    "ዛሬ ጠዋት በርካታ የአሜሪካ ተዋጊ አውሮፕላኖች ተከስክሰዋል" ሲል የኩዌት የመከላከያ ሚኒስቴር አስታወቀ።

    የበረራ አባላቱ "ምንም ጉዳት ሳይደርስባቸው በሕይወት ተርፈዋል" በማለት ወደ ሆስፒታሎች መወሰዳቸውን መግለጫው አክሎ ገልጿል።

    የኩዌት መከላከያ ሚኒስቴር መግለጫ የበረራ አባላቱ ሁኔታ "የተረጋጋ" መሆኑን አስታውቋል።

    የመከላከያ ሚኒስቴር አክሎም ከአሜሪካ ጋር ስለ "ክስተቱ" እየተነጋገረ መሆኑን እና "የክስተቱን መንስዔዎች" በተመለከተ ምርመራውን እየተካሄደ መሆኑን አስታውቋል።

  19. ዩኬ፣ ፈረንሳይ እና ጀርመን በቀጣናው “ጥቅሞቻችን ለማስጠበቅ እርምጃ ለመውሰድ” ዝግጁ ነን አሉ

    የብሪታኒያ ጠቅላይ ሚኒስትር ኬይ ስታርመር

    የፎቶው ባለመብት, X / Keir Starmer

    የምስሉ መግለጫ, የብሪታኒያ ጠቅላይ ሚኒስትር ኬር ስታርመር፤ ከኢራንን "ስጋቶች ለማስቆም ብቸኛው መፍትሔ ሚሳዔሎቹን ከምንጫቸው ማጥፋት" እንደሆነ ተናግረዋል

    ዩናይትድ ኪንግደም፣ ፈረንሳይ እና ጀርመን በጋራ ባወጡት መግለጫ ኢራን በጎረቤቶቿ ላይ የፈጸመችውን "ያልተመጣጠነ እና የዘፈቀደ የሚሳዔል" ጥቃት አውግዘዋል።

    ዩናይትድ ኪንግደም በበኩሏ አሜሪካ የብሪታኒያን የጦር ሰፈሮች ተጠቅማ የመከላከያ እርምጃ እንድትወስድ ልትፈቅድ መሆኑን አስታውቃለች።

    የብሪታኒያ ጠቅላይ ሚኒስትር ኪር ስታርመር፣ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን እና የጀርመኑ ቻንስለር ፍሪድሪሽ ሜርዝ ኢራን ጥቃት መፈጸሟን እንድታቆም ጠይቀዋል። አገራቱ በመካከለኛው ምሥራቅ ያላቸውን ጥቅሞች ለማስጠበቅ አስፈላጊውን እርምጃ ለመውሰድ ዝግጁ መሆናቸውን ገልጸዋል።

    "የራሳችንን እና በቀጠናው ያሉ አጋሮቻችንን ፍላጎቶች ለመከላከል እርምጃዎችን እንወስዳለን። ይህም የኢራንን ሚሳዔሎች እና ድሮኖች የመተኮስ አቅሟ ከምንጩ የሚያጠፋ አስፈላጊ እና ተመጣጣኝ የመከላከያ እርምጃ ሊሆን ይችላል" ብለዋል።

    የዩናይትድ ኪንግደም ጠቅላይ ሚኒስትር ስታርመር በቪዲዮ ባስተላለፉት መልዕክት፤ አሜሪካ የአገሪቱን የጦር ሰፈሮች እንድትጠቀም እንደሚፈቅዱ ገልጸዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ “በባሕረ ሰላጤው የሚገኙ አጋሮቻችን እነርሱን ለመከላከል ተጨማሪ ተግባር እንድናከናውን ጠይቀውናል… በተቀናጀው የመከላከያ ዘመቻ አካል የሆኑ የብሪታኒያ ጄቶች አየር ላይ አሉን…አስቀድሞም በተሳካ ሁኔታም የኢራንን ጥቃቶች አክሽፈዋል” ብለዋል።

    “ነገር ግን ስጋቶቹን ለማስቆም ብቸኛው መንገድ ሚሳዔሎቹን ከምንጫቸው ማጥፋት፤ እዚያው ከማከማቻ ዴፗቸው ወይም ሚሳኤል ለመተኮስ ጥቅም ላይ ከሚውሉት ማስወነጨፊያዎች” ሲሉም ተናግረዋል።

    "ኢራን በመላ ቀጣናው ሚሳዔል እየተኮሰች ንጹሃንን እንዳትገድል፣ የብሪታኒያውያንን ሕይወት አደጋ ላይ እንዳትጥል እና ተሳትፎ የሌላቸውን አገራት እንዳትመታ ለመከላከል የቀረበልንን ጥያቄ ለመቀበል ወስነናል” ሲሉ የአገራቸው አቋም ገልጸዋል።

  20. አሜሪካ በ24 ሰዓታት ውስጥ ከአንድ ሺህ በላይ ዒላማዎችን መምታቷን አስታወቀች

    በኢራን ላይ ጥቃት

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    በኢራን ላይ የጥቃት ዘመቻ ከተጀመረ በኋላ ባሉት በመጀመሪያዎቹ 24 ሰዓታት ከአንድ ሺህ በላይ ዒላማዎች ኢራን ውስጥ መመታታቸውን የዩናይትድ ስቴትስ ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንትኮም) አስታወቀ።

    ዕዙ ካወጣው የጥቃት ዝርዝር ውስጥ ነጥሎ መቺ ቦምብ ጣይ አውሮፕላኖች፣ ድሮኖች፣ ተዋጊ ጄቶች እና ፀረ ሚሳዔል ሥርዓቶችን ጨምሮ የአሜሪካ ሠራዊት ጥቅም ላይ ያዋላቸው ጦር መሳሪያዎችንም አካትቷል።

    ማዕከላዊ ዕዙ ዒላማ ከተደረጉት ከአንድ ሺህ በላይ ዒላማዎች መካከል የኢራን የማዘዣ እና መቆጣጠሪያ ማዕከላት፣ የባለስቲክ ሚሳዔል ማስወንጨፊያ ቦታዎች እና የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ዋና ጽህፈት ቤት ይገኙበታል።

    የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ የተፈጸመው ጥቃት “በከፍተኛ ሁኔታ ወሳኝ ውጤትን” አስገኝቷል በማለት የእስራኤል መከላከያ ኃይል የሰጠውን አስተያየት ደግሞታል።