ቀጥታ, የአሜሪካ ባሕር ኃይል የኢራን ጦር መርከብን በሚሳዔል መትቶ ሲያሰምጥ ቢያንስ የ80 ሰዎች ሕይወት አለፈ

የአሜሪካ የመከላከያ ሚኒስትር ፔት ሄግሴት የአሜሪካ ጦር ኃይል በሕንድ ውቅያኖስ ላይ አንድ “የኢራን የጦር መርከብ” በውሃ ውስጥ የሚምዘገዘግ ሚሳዔል በመጠቀም ማስመጡን ተናግረዋል። በኢራን የጦር መርከብ ላይ የነበሩ 80 ሰዎች አስከሬን መገኘቱን ደግሞ የሲሪላንካ መከላከያ ሚኒስቴር ምክትል ሚኒስትር ማርሻል ሳምፓዝ ቱያኮንታ ለቢቢሲ ሲንሃላ ተናግረዋል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. “አሁን ከአሜሪካ ጋር መደራደር ውጤታማነቱ አጠራጣሪ ነው”- ኢራን

    በተባበሩት መንግሥታት የኢራን አምባሳደር የሆኑት አሊ ባህሬኒ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የምስሉ መግለጫ, በተባበሩት መንግሥታት የኢራን አምባሳደር አሊ ባህሬኒ

    በተባበሩት መንግሥታት የኢራን አምባሳደር የሆኑት አሊ ባህሬኒ፤ ከአሜሪካ ጋር አሁን ላይ ድርድር ማድረግ “ውጤታማነቱ አጠራጣሪ ነው” አሉ።

    ቀደም ሲል የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ፤ የኢራን ባለሥልጣናት ከአሜሪካ ጋር የመነጋገር ፍላጎት እንዳላቸው፤ ነገር ግን ጊዜው እንዳለፈባቸው እንደነገሯቸው ገልጸዋል።

    የኢራኑ አምባሳደር በበኩላቸው “ከአሜሪካ ጋር ድርድር ማድረግ ውጤታማነቱ ላይ ከፍተኛ ጥርጣሬ አለን” ማለታቸውን ሮይተርስ የዜና ወኪል ዘግቧል።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት መልዕክት የኢራን ወሳኝ ተቋማት እና መሪዎች መመታታቸውን ጠቅሰው “ለንግግር ጊዜው አልፏል” ማለታቸው ይታወሳል።

    አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ ጦርነት መክፈታቸውን ተከትሎ ኢራን የአጸፋ እርምጃ መውሰዷን ቀጥላለች።

    የኢራን እስላማዊው አብዮታዊ ዘብ ቃል አቀባይ ብርጋዴር ጄነራል አሊሞሐማድ ናኢም፤ በአሜሪካ እና በእስራኤል ላይ “የሲኦል በሮች ይከፈታሉ” ብለው ዝተዋል።

  2. ኢራን፤ በኩዌት ወታደራዊ ሰፈር በፈጸመችው ጥቃት ስድስት የአሜሪካ ወታደሮች ተገደሉ

    በኩዌት የሚገኘው የአሜሪካ ወታደራዊ መቀመጫ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ኢራን እሑድ ዕለት በኩዌት በሚገኝ የአሜሪካ ወታደራዊ ሰፈር ላይ በፈጸመችው ጥቃት ስድስት አሜሪካውያን ወታደሮች መገደላቸው ተረጋገጠ።

    የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ ከዚህ ቀደም ባወጣው መግለጫ ሦስት ወታደሮች መሞታቸውን አስታውቆ ነበር።

    ተጎድቶ የነበረ ወታደር ከሞተ እና ሁለት ተጨማሪ ወታደሮች አስከሬናቸው ከፍርስራሽ ሥር ከተገኘ በኋላ የሟቾች ቁጥር ስድስት ደርሷል።

    የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር ፒት ሄግዜት እንደተናገሩት፤ ኢራን በኩዌት በሚገኝ የአሜሪካ ወታደራዊ ሰፈር ላይ የአጸፋ ጥቃት ሰንዝራለች።

    አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ ጦርነት ከከፈቱ ወዲህ በኩዌት የተገደሉት ስድስት አሜሪካውያን ብቻ መሆናቸው ተገልጿል።

    “ኃይለኛ መሣሪያ የታክቲክ ኦፕሬሽን ማዕከል ላይ ተተኩሷል” ሲሉ የመከላከያ ሚስሩ ተናግረዋል።

    የቢቢሲ የአሜሪካ አጋር ሲቢኤስ ያነጋገራቸው የአሜሪካ ወታደራዊ ባለሥልጣት እንደገለጹት፤ ወታደሮቹ በኩዌት ጊዜያዊ ቢሮ ውስጥ ነበሩ።

    በባሕረ ሰላጤው አገራት ወታደራዊ ሰፈሮች ያሏት አሜሪካ በኩዌትን 13,000 ወታደሮች አስፍራለች።

    ኢራን እየወሰደች ባለችው የአጸፋ እርምጃ ባህሬን፣ የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች፣ ሳዑዲ አረቢያ፣ ኦማን እና ኳታር ላይ ጥቃት ፈጽማለች።

  3. "ኢራኖች መነጋገር ቢፈልጉም፣ እኔ 'በጣም ዘገያችሁ!' አልኳቸው"- ፕሬዝዳንት ትራምፕ

    ትርምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ፤ የኢራን ባለሥልጣናት ከአሜሪካ ጋር የመነጋገር ፍላጎት እንዳላቸው፤ ነገር ግን ጊዜው እንዳለፈባቸው እንደነገሯቸው ገለጹ።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት መልዕክት የኢራን ወሳኝ ተቋማት እና መሪዎች መመታታቸውን ጠቅሰው ነው ለንግግር ጊዜው እንዳለፈ የጻፉት።

    "የአየር መከላከያቸው፣ የአየር እና የባሕር ኃይላቸው እንዲሁም አመራራቸው በሙሉ የሉም” ሲሉ ነው ፕሬዝዳንቱ የጻፉት።

    ፕሬዝዳንቱ ይህንን ጽሑፍ ዋሽንግተን ፖስት ላይ ከወጣ “የትራምፕ መርኅ መወለድ” በሚል ርዕስ ከወጣ ጽሑፍ ሊንክ ጋር አያይዘው ነው ያሰፈሩት።

    "እነሱ መነጋገር ፈልገው ነበር፤ እኔ ግን ‘በጣም ዘገየ!’ አልኳቸው” ሲሉ ጽፈዋል።

  4. በአሜሪካ እና በእስራኤል ላይ “የሲኦል በሮች ይከፈታሉ” - የኢራን አብዮታዊ ዘብ

    ብርጋዴር ጄነራል አሊሞሐማድ ናኢም

    የፎቶው ባለመብት, Tasnim News Agency

    የምስሉ መግለጫ, ብርጋዴር ጄነራል አሊሞሐማድ ናኢም

    የኢራን መንግሥት ዋነኛው ወታደራዊ ኃይል እስላማዊው አብዮታዊ ዘብ በአሜሪካ እና በእስራኤል ላይ “የሲኦል በሮች ይከፈታሉ” ሲል ዛተ።

    መሪው ቴህራን ውስጥ በተፈጸመ ጥቃት የተገደሉበት የአብዮታዊ ዘብ ቃል አቀባይ ብርጋዴር ጄነራል አሊሞሐማድ ናኢም “ጠላት” ባሏቸው በእስራኤል እና በአሜሪካ ላይ ሠራዊታቸው ቀጣይነት ያለው ጥቃት እንደሚፈጽም ተናግረዋል።

    ጄነራሉ ታስኒም ለተባለው የአገሪቱ ዜና ወኪል በሰጡት ቃል ኢራን ለተከፈተባት ጥቃት በታጠቀቻቸው ዘመናዊ ሚሳዔሎች “የሲኦል በሮች በአሜሪካ እና በእስራኤል ላይ በከፍተኛ ሁኔታ ይከፈታሉ” ብለዋል።

    አራተኛ ቀኑን በያዘው እና ኢራን ለተፈጸመባት ጥቃት በእስራኤል እንዲሁም በመካከለኛው ምሥራቅ ውስጥ በሚገኙ የአሜሪካ ወዳጅ አገራት ላይ የምትፈጽመውን የሚሳዔል እና የድሮን ጥቃቶችን ቀጥላለች።

    አብዮታዊ ዘቡም አዲስ በተሾሙለት አዛዡ አሕመድ ቫሂዲ መሪነት ተልዕኮውን በሙሉ ኃይሉ ያለማቋረጥ በመቀጠል ጠላቶቹን እንደሚበቀል ቃል አቀባዩ ተናግረዋል።

    በአሜሪካ እና በእስራኤል ዋነኛ ዒላማ ከተደረጉት የኢራን ወታደራዊ ተቋማት መካከል አንዱ የሆነው አብዮታዊው ዘብ አዛዦች እና አባላት የተገደሉባቸውን “ሰማዕታቶች ደም” በመበቀል “ጠላቶቻችንን አሳፋሪ ሽንፈት እናከናንባቸዋለን” ብለዋል ብ/ጄነራል አሊሞሐማድ።

  5. እስራኤል በኢራን ፕሬዝዳንት ጽሕፈት ቤት ላይ ጥቃት ፈጸመች፤ እስካሁን 787 ሰዎች መገደላቸው ተገለጸ

    ጥቃት የተፈጸመበት ጋንዲ ሆስፒታል

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ጥቃት የተፈጸመበት ጋንዲ ሆስፒታል

    የእስራኤል መከላከያ ኃይል የቴህራን አመራሮች በሚገኙበት አካባቢ በፈጸመው የአየር ድብደባ የፕሬዝዳንቱ ጽሕፈት ላይ ጉዳት ማድረሱን አስታወቀ።

    የእስራኤል መከላከያ በቴግራም ገጽ ላይ ባወጣው መግለጫ፤ በፕሬዝዳንቱ ጽሕፈት ቤት እና በኢራን ከፍተኛ ብሔራዊ ደኅንነት ምክር ቤት ላይ “በርካታ ድብደባ” መፈጸሙን አስታውቋል።

    ወታደራዊ የሥልጠና ተቋማት እና ሌሎችም “የኢራን መንግሥት ቁልፍ መሠረተ ልማቶች” ላይ ጥቃት መድረሱም ተገልጿል።

    በእስራኤል እና በአሜሪካ ጥቃት የተገደሉት የኢራን ጠቅላይ መሪ አያቶላህ አሊ ኻሜኒ ሥራቸውን ያከናውኑ የነበረው አሁን ድብደባ በደረሰበት ቅጥር ጊቢ ውስጥ እንደነበር የእስራኤል መከላከያ አመልክቷል።

    በተያያዘም፤ እስራኤል እና አሜሪካ ኢራን ላይ ጥቃት መፈጸም ከጀመሩበት ቀን አንስቶ ቢያንስ 787 ሰዎች መገደላቸውን የኢራን ቀይ ጨረቃ ማኅበር አስታውቋል።

    ‘ሂውማን ራይትስ አክቲቪስትስ ኢን ኢራን’ የተባለው የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅት እንዳለው 176 ሕጻናትን ጨምሮ 742 ሰዎች ተገድለዋል።

    የኢራን ምክር ቤት የጤና ኮሚሽን አባል የሆኑት ፋጢማ ሞሐመድባጊ እንደተናገሩት፤ ትናንት ሰኞ ዘጠኝ ሆስፒታሎች በእስራኤል እና አሜሪካ ጥቃት ዒላማ ተደርገዋል።

    የእስራኤል መከላከያ በበኩሉ በቴህራን የጋንዲ ሆስፒታል ላይ ጥቃት ፈጽሟል የሚለውን ክስ አስተባብሎ “ሆስፒታሉ ዒላማ አልተደረገም” ብሏል።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ዛሬ ባወጣው መግለጫ እስራኤል እና አሜሪካ በዚህ ሆስፒታል ላይ አነጣጥረው ጥቃት ማድረሳቸውን አስታውቋል።

  6. በኢራን የሟቾች ቁጥር 787 መድረሱን ቀይ ጨረቃ አስታወቀ

    የእስራኤል ጥቃት በቴህራን

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    እስራኤል እና አሜሪካ በጥምረት ባለፈው ቅዳሜ ጥቃት መፈጸም ከጀመሩ ወዲህ የሞቱት ኢራናውያን ቁጥር 787 መድረሳቸውን የቀይ ጨረቃ አስታወቀ።

    በሌላ በኩል መቀመጫውን አሜሪካ ያደረገው የሰብዓዊ መብት ቡድን ያወጣው መረጃ ደግሞ 176 ሕጻናትን ጨምሮ 742 ሰላማዊ ሰዎች መገደላቸውን ይፋ አድርጓል።

    ፋተሜህ ሞሃማድቤጊ የተባሉ የኢራን የፓርላማ አባል እንደገለጹት ደግሞ የአሜሪካ እና የእስራኤል ጥቃት በኢራን ውስጥ ዘጠኝ ሆስፒታሎችን ዒላማ አድርገዋል።

    የእስራኤል መከላከያ ኃይል ቴህራን ውስጥ የጋንዲ ሆስፒታልን ዒላማ ስለማድረጉ ተጠይቆ “ዒላማችን ሆስፒታሉ አልነበረም” የሚል ምላሽ ሰጥቷል።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሆስፒታሉ በእስራኤል ጥቃት ዒላማ መሆኑን ገልጿል።

  7. እስራኤል በቤይሩት በፈጸመችው ጥቃት የደረሰውን ውድመት የሚያሳይ ምስል

    እስራኤል ዛሬ በአገሬው ሰዓት አቆጣጠር ከጠዋቱ 2፡00 ጀምሮ በቤይሩት እና ቴህራን ጥቃት መፈጸሟን ቀጥላለች።

    እስራኤል በሁለቱም አገራት “ወታደራዊ ዒላማዎች” ናቸው ባለቻቸው ስፍራዎች የአየር ድብደባ ማካሄዷን ተናግራለች።

    ሊባኖስ ውስጥ በኢራን የሚደገፈው ሔዝቦላህ ዒላማዎች ናቸው ባለቻቸው ስፍራዎች ነው ጥቃቶቹን የፈጸመችው።

    ቤይሩት ውስጥ የተፈጸሙት ጥቃቶች ያደረሷቸውን ጉዳቶች የሚያሳዩ ምስሎች እነሆ።

    በደቡባዊ ቤይሩት የእስራኤል ጦር በፈጸመው ጥቃት የወደመ ሕንጻ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, በደቡባዊ ቤይሩት የእስራኤል ጦር በፈጸመው ጥቃት የወደመ ሕንጻ
    በደቡባዊ ቤይሩት በጥቃቱ የወደመን ስፍራ የሚመለከት ሰው

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, በደቡባዊ ቤይሩት በጥቃቱ የወደመን ስፍራ የሚመለከት ሰው
    በቤይሩት በመኖሪያ ስፍራ የተፈጸመን ጥቃት ተከትሎ የተቀሰቀሰ የእሳት ቃጠሎን የሚያጠፉ የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, በቤይሩት በመኖሪያ ስፍራ የተፈጸመን ጥቃት ተከትሎ የተቀሰቀሰ የእሳት ቃጠሎን የሚያጠፉ የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች
  8. አራተኛ ቀኑን በያዘው አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ የከፈቱት ጦርነት ዐበይት ክስተቶች

    እስራኤል በቤይሩት የፈጸመችውን የአየር ድብደባ ተከትሎ የተፈጠረ ጭስ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    አራተኛ ቀኑን የያዘው በአሜሪካ እና በእስራኤል ጥቃት የተጀመረው የመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት በርካታ የአካበቢውን አገራት ለኢራን ጥቃት አጋልጦ ቀጥሏል።

    • ዛሬ ማክሰኞ ከማለዳ ጀምሮ እስራኤል በቴህራን እና ቤይሩት “ወታደራዊ ዒላማዎች” ባለቻቸው ስፍራዎች ላይ “ተከታታይ የአየር ጥቃቶች” እየፈጸመች መሆኑን አስታውቃለች።
    • የሳዑዲ መከላከያ ሚኒስቴር በሪያድ በሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ ላይ በሁለት ድሮኖች ጥቃት መፈጸሙን እና መጠነኛ ጉዳት መድረሱን ገልጿል።
    • የኢራን መንግሥት መገናኛ ብዙኃን በባህሬን በሚገኘው የአሜሪካ አየር ኃይል ማዘዣ እና የሠራተኞች ሕንጻ ላይ ጥቃት መድረሱን ዘግበዋል።
    • የአሜሪካው ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ማርኮ ሩቢዮ የአገሪቱ ጦር በኢራን ላይ የሚፈጽመው "ከባዱ ጥቃት ገና እየመጣ ነው" ሲሉ አስጠንቅቀዋል።
    • ጦርነቱ ከጀመረ ጊዜ አንስቶ ስድስት የአሜሪካ ወታደሮች ተገድለዋል።
    • በኩዌት የሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ በቀጠናው የተፈጠረን ውጥረት በመጥቀስ ዝግ መሆኑን አስታውቋል።
    • እስራኤል ወደ ሊባኖስ እግረኛ ጦሯን በማስገባት "ተጨማሪ ቁልፍ ስፍራዎችን" ልትቆጣጣር መሆኑን አስታውቃለች።
    • የዩኬው ጠቅላይ ሚኒስትር ሰር ኪር ስታርመር መንግሥታቸው ጥቃትን ተከትሎ በኢራን በሚመጣ የመንግሥት ለውጥ እንደማያምን ተናግረዋል። ዶናልድ ትራምፕ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ተባባሪ አይደሉም ሲሉ ከስሰዋል።
  9. በኦማን ወደብን ዒላማ ያደረገ የድሮን ጥቃት ተፈጸመ

    በጭስ የተሸፈነ የኦማን ወደብ

    የፎቶው ባለመብት, UGC

    የምስሉ መግለጫ, ጥቃት የተፈጸመበት አካባቢ

    በኦማን የንግድ ወደብ ላይ የድሮን ጥቃት መፈጸሙን የአገሪቱ መንግሥት የዜና ወኪል ዘገበ።

    ጥቃቱ የተፈጸመው ዱቅም በሚባለው የንግድ ወደብ ላይ ሲሆን፣ አንድ ነዳጅ ማጠራቀሚያ ጋን ዒላማ መደረጉ ተዘግቧል።

    ማንነቱን እንዲገለጽ ያልፈለገ በአካባቢው ያለ የደኅንነት ምንጭ “ጥቃቱ በሰው ላይ ጉዳት ሳያደርስ መቆጣጠር ተችሏል” ብሏል።

    ባለፈው ሳምንት መጨረሻ ላይ ወደቡ በድሮን ጥቃት ዒላማ ተደርጎ ነበር። በጥቃቱም አንድ የወደቡ ሠራተኛ ጉዳት እንደደረሰበት ተነግሯል።

    በኳታር ሰኞ ዕለት የተፈጥሮ ጋዝ ማጣሪያ በኢራን ጥቃት በመመታቱ የተወሰነ ክፍሉ መጎዳቱን ተከትሎ ሥራ አቋርጦ ነበር። የሳዑዲ አረቢያም ዋነኛ የነዳጅ ማጣሪያ በዚሁ ጦርነት ምክንያት ለጊዜው ሥራ እንዲያቆም አድርጋለች።

    አሁን በኢራን ጥቃት የተመታችው ኦማን ኢራን እና አሜሪካን ለዓመታት በማደራደር ቁልፍ ሚና ነበረት። በቅርቡ በሦስት ዙር የተደረገው ድርድርም የተጀመረው ኦማን ውስጥ ነበር።

  10. አሜሪካ ዜጎቿ ከ14 አገራት በአስቸኳይ ለቅቀው እንዲወጡ አዘዘች

    የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ዜጎቹ በመካከለኛው ምሥራቅ ከሚገኙ 14 አገራት በአስቸኳይ ለቅቀው እንዲወጡ አዘዘ።

    የአገሪቱ የቆንስላ ጉዳዮች ረዳት ሚኒስቴር የሆኑት ሞራ ናምዳር በመሥሪያ ቤታቸው የማኅበራዊ ሚዲያ ገጾች ላይ ባሰፈሩት መልዕክት አሜሪካውያን “ሊያጋጥሙ በሚችሉ ከባድ አደጋዎች ምክንያት” ከአስራ አራቱ አገራት “ያሉ የትራንስፖርት አመራጮችን በመጠቀም አሁኑኑ” ለቅቀው እንዲወጡ አሳስበዋል።

    የአሜሪካ ዜጎች በአስቸኳይ ለቅቀው እንዲወጡ የታዘዙባቸው አገራት ባህሬን፣ ግብፅ፣ ኢራን፣ ኢራቅ፣ እስራኤል፣ የፍልስጤም ግዛቶች፣ ዮርዳኖስ፣ ኩዌት፣ ሊባኖስ፣ ኦማን፣ ኳታር፣ ሳዑዲ አረቢያ፣ ሶሪያ፣ የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ እና የመን ይገኙባቸዋል።

    በኩዌት የሚገኘው ኤምባሲ ለየትኛውም የቆስንስላ ጉዳዮች የሚሰጠውን አገልግሎት ማቋረጡን ማስታወቁ ይታወሳል።

  11. ትራምፕ የዩኬውን ጠቅላይ ሚኒስትር “ተባባሪ አይደሉም” ሲሉ ተቹ

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ትራምፕ እና ኪር ስታርመር

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    አሜሪካ በኢራን ላይ በምትፈጽመው ጥቃት ዙሪያ የዩኬ ጠቅላይ ሚንስትር ያሳዩትን አቋም ፕሬዝዳንት ትራምፕ “አጋዥ አይደሉም፤ ግንኙነታችንም እንደድሮው አይደለም” በማለት ተቹ።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ለ ዘ ሰን እንደተናገሩት “ጠቅላይ ሚንስትሩ ተባባሪ አይደሉም። ይህ ይሆናል ብዬ አስቤ አላውቅም። ከዩናይትድ ኪንግደም ይህንን አልጠብቅም ነበር” ብለዋል።

    በስልክ ባደረጉት ቃለ መጠይቅ “ከዩናይትድ ኪንግደም እንደዚህ ዓይነት ነገር መመልከት እና ግንኙነታችን እንደ ቀድሞው አለመሆን በጣም አሳዛኝ ነው” ብለዋል።

    ሰኞ ዕለት ጠቅላይ ሚኒስትር ኪር ስታርመር ለምክር ቤት አባሎቻቸው “በኃይል የሚቀየርን መንግሥት አላምንበትም” ብለው ነበር።

    ዩናይትድ ኪንግደም መጀመሪያ ላይ አሜሪካ ኢራንን እንድታጠቃ የጦር ሰፈሯን አልፈቀደችም ነበር። በኋላ ላይ ግን ለመከላከል አገልግሎት መፍቀዷን ገልጻለች።

    ትራምፕ በቃለ መጠይቃቸው “ፈረንሳይ ጥሩ እየሠራች ነው። ሌሎቹ ሁሉም ጥሩ ናቸው። ከሌሎቹ በእጅጉ የተለየችው ዩናይትድ ኪንግደም ነች” ብለዋል።

  12. በዩኔስኮ የተመዘገበው የቴህራኑ ጎሌስታን ቤተ መንግሥት ጥቃት ደረሰበት

    በዩኔስኮ በቅርስነት የተመዘገበው የጎሌስታን ቤተ መንግሥት

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, በዩኔስኮ በቅርስነት የተመዘገበው የቴህራኑ ጎሌስታን ቤተ መንግሥት ጥቃት ደረሰበት

    በኢራን ዋና ከተማ የሚገኘው ታሪካዊው እና በዩኔስኮ በቅርስነት የተመዘገበው የጎሌስታን ቤተ መንግሥት በመዲናዋ በተፈጸመው ጥቃት ጉዳት ደረሰበት።

    የደረሰውን ጉዳት ተከትሎ ዩኔስኮ ለቅርሶች የሚደረገው ጥበቃ እንዳሳሰበው ገልጿል።

    የአገር ውስጥ መገናኛ ብዙኃን እንደዘገቡት ከቤተ መንግሥቱ አቅራቢያ አርግ አደባባይ ላይ ፍንዳታ ተከስቷል።

    የጎሌስታን ቤተ መንግሥት በቃጃር ስርወ መንግሥት ዘመን የኢራን ንጉሳውያን ቤተሰቦች መኖሪያ የነበረ ሲሆን በኋላ ላይ ደግሞ የፓህላቪ ስርወ መንግሥት ዋና መኖሪያ ነበር።

  13. እስራኤል ወደ ሊባኖስ እግረኛ ጦሯን በማስገባት “ተጨማሪ ቁልፍ አካባቢዎችን” እንደምትይዝ ገለፀች

    እስራኤል ዛሬ ማለዳ በቤሩት የፈጸመችውን ጥቃት ተከትሎ የተነሳ ጭስ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, እስራኤል ዛሬ ማለዳ በቤሩት የፈጸመችውን ጥቃት ተከትሎ የተነሳ ጭስ

    የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ ጦሩ ወደ ሊባኖስ ገብቶ “ተጨማሪ ቁልፍ አካበቢዎችን” እንዲቆጣጠር ማዘዛቸውን የአገሪቱ መከላከያ ሚኒስትር እስራኤል ካትዝ ገለፁ።

    የእስራኤል እግረኛ ጦር ወደ ሊባኖስ እንዲገባ የታዘዘው በእስራኤል ድንበር አካባቢ የሚገኙ ማኅበረሰቦች ላይ የሚተኮሰውን ሮኬት ለመከላከል በሚል ነው።

    የእስራኤል ጦር በሊባኖስ በሚገኙ የሔዝቦላህ ዒላማዎች ላይ የሚወስደውን የኃይል እርምጃ አጠናክሮ እንደሚቀጥል ሚኒስትሩ ተናግረዋል።

    “አሸባሪው ድርጅት ወደ እስራኤል በሚያስወነጭፈው ሮኬት የተከሳ ዋጋ እየከፈለ ነው፤ መክፈሉንም ይቀጥላል” ብለዋል።

    የእስራኤል መከላከያ ሚኒስትር እስራኤል ካትዝ “በድንበር የሚገኙ ማኅበረሰቦችን ለመከላከል” ቁርጠኛ ነን ብለዋል።

    “በጋሊሊ የሚገኙ ማኅበረሰቦችን ደህንነት ለመከላከል ቃል ገብተናል፤ እያደረግንም ያለነው ያንን ነው” ብለዋል።

  14. በኩዌት የሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ ተዘጋ

    በኩዌት የሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ “ተጨማሪ መግለጫ እስኪሰጥ ድረስ” በሚል “በቀጠናው ያለውን ውጥረት” በመጥቀስ መዘጋቱን በኤክስ ገጹ ላይ ባስተላለፈው መልዕክት አስታወቀ።

    ኤምባሲው “መደበኛ እና አስቸኳይ የሆኑ የቆንስላ ቀጠሮዎችን በሙሉ ዘግተናል” ብሏል።

    ሰኞ ዕለት የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ኩዌትን ጨምሮ በመካከለኛው ምሥራቅ የሚኖሩ አሜሪካውያን በፍጥነት ለቅቀው እንዲወጡ አስታውቆ ነበር።

    ሚኒስቴሩ ይህንን ያለው “ከፍተኛ የሆነ የደህንንት አደጋ” በመኖሩ እንደሆነ በመግለጫው ላይ አስታውቆ፣ ባለው የመውጫ መንገድ ሁሉ አገራቱን ለቅቀው አንዲወጡ አሳስቦ ነበር።

    ሰኞ ዕለት በኩዌት ሦስት የአሜሪካ ጦር ጄቶች ተከስክሰዋል። አሜሪካ ተዋጊ አውሮፕላኖቿ በኩዌት የወደቁት ኢራን ላይ የተከፈተውን ጥቃት ሲያከናውኑ በተፈጠረ ድንገተኛ ክስተት እንጂ ጥቃት ደርሶባቸው እንዳልሆነ አስታውቃለች።

    አሜሪካ የኩዌት ኤምባሲዋን የዘጋችው በሪያድ የሚገኘው ኤምባሲዋ በሁለት ድሮኖች ጥቃት ከደረሰበት በኋላ ነው።

  15. ሔዝቦላህ ሦስት የእስራኤል ወታደራዊ ቦታዎችን ማጥቃቱን ገለጸ

    ሔዝቦላህ በሦስት የተለያዩ የእስራኤል ወታደራዊ ቦታዎች ላይ ጥቃት መፈጸሙን አስታወቀ።

    በኢራን የሚደገፈው ሔዝቦላህ እስራኤል በበርካታ የሊባኖስ ከተሞች እና አካባቢዎች ላይ ለምትፈጽመው ጥቃት እና ወረራ “ምላሽ ሰጥቻለሁ” ብሏል።

    በሦስት የተለያዩ የቴሌግራም ልጥፎች በጎላን ተራሮች የሚገኘውን ናፋህ የጦር ሰፈር፣ ሜሮን እና ራማት ዴቪድ የአየር ኃይል የጦር ቦታዎችን በሚሳኤል እና በድሮን ማጥቃቱን ሔዝቦላህ ገልጿል።

    ሔዝቦላህ ፈጸምኩት ላለው ጥቃት እስራኤል የሰጠችው አስተያየት የለም።

  16. ሰበር, በሪያድ የሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ የድሮን ጥቃት ደረሰበት

    የሳዑዲ አረቢያ መከላከያ ሚኒስቴር በሪያድ በሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ ላይ ጥቃት መፈጸሙን አስታወቀ።

    ሚኒስቴሩ በኤምባሲው ላይ ጥቃት የደረሰው በሁለት ድሮኖች መሆኑን ጨምሮ ገልጿል።

    ሚኒስቴሩ በኤክስ ገጹ ላይ ባሰፈረው መልዕክት ጥቃቱ “መጠነኛ እሳት እና በሕንጻው ላይ አነስተኛ የንብረት ጉዳት” ማድረሱን ገልጿል።

    በሳዑዲ አረቢያ የሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ በጂዳ፣ ሪያድ እና ዳሃራን የሚገኙ አሜሪካውያን ደህንታቸው በተጠበቁ ስፍራዎች እንዲቀዩ ያሳሰበ ሲሆን በቀጠናው በሚገኙ ወደየትኛውም የጦር ካምፖች የሚደረግ አላስፈላጊ ጉዞን እንዲያስወግዱ መክሯል።

  17. አሜሪካ “ለተራዘመ” ጦርነት የሚበቃ የጦር መሣሪያ ክምችት እንዳላት ትራምፕ ተናገሩ

    ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በትሩዝ ሶሻል የማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ አገራቸው “የተራዘመ ጦርነት” ማድረግ የሚያስችሉ የ"መካከለኛ እና ከፍተኛ ደረጃ" የጦር መሣሪያዎች እንዳላት በመግለጽ በእነዚህ አቅርቦቶች ብቻ መዋጋት እንችላለን አሉ።

    "የእነዚህ የጦር መሣሪያዎች ከፍተኛ ክምችት አለን። ዩናይትድ ስቴትስ በቂ ክምችት አላት። እና ለማሸነፍ ዝግጁ ናት. . . " ሲሉ ትራምፕ በማኅበራዊ ድረገጻቸው ላይ ጽፈዋል።

    ዶናልድ ትራምፕ በቅርቡ በሰጡት አስተያየት ጆ ባይደን ለዩክሬን "እጅግ በጣም ከፍተኛ" የሆነ የአሜሪካን የጦር መሣሪያ በመስጠታቸው ተችተዋል።

    ባይደን የአራት ዓመት የሥልጣን ዘመናቸው ማብቂያ ላይ ለዩክሬን እስከ 300 ኪ.ሜ ድረስ የሚወነጨፉ ኤቲኤሲኤምኤስ (ATACMS) የተባለ የረጅም ርቀት ተምዘግዛጊ ሚሳዔሎችን ሰጥተው ነበር።

  18. የዩኬ ጠቅላይ ሚኒስትር መንግሥታቸው "በጥቃት በሚመጣ የመንግሥት ለውጥ አያምንም" አሉ

    የዩኬ ጠቅላይ ሚኒስትር ሰር ኪር ስታርመር

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የዩኬ ጠቅላይ ሚኒስትር ሰር ኪር ስታርመር ለፓርላማ አባላት መንግሥታቸው "በጥቃት በሚመጣ የመንግሥት ለውጥ" እንደማያምን ተናገሩ። ይህም ከእስራኤል ጋር በመሆን ኢራን ላይ ጥቃት ከከፈቱት ትራምፕ በተቃራኒ እንዲቆሙ አድርጓቸዋል።

    የዩኬ ጠቅላይ ሚኒስትር ኢራን ላይ ጥቃት ከተፈጸመ ወዲህ ባደረጉት የመጀመርያ የፓርላማ ንግግራቸው፣ አሜሪካ የዩኬን ጦር ሠፈር እንድትጠቀም መፍቀዳቸው ተገቢ እንደነበር በመግለጽ ተከላክለዋል።

    "ከፕሬዚዳንት ትራምፕ ጋር በመጀመሪያ ጥቃቶች ላይ ላለመሳተፍ በመወሰናችን አልተግባብንም ነበር፤ ነገር ግን የብሪታኒያ ብሔራዊ ጥቅም ምን እንደሆነ የመወሰን የእኔ ኃላፊነት ነው" ሲሉ ለፓርላማ አባላት ተናግረዋል።

    ነገር ግን እሁድ ዕለት ሁኔታዎች ተቀየሩ ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ የኢራን "ተገቢ ያልሆነ" ምላሽ "ለሕዝባችን እና ለፍላጎታችን እንዲሁም ለአጋሮቻችን ስጋት ሆነ" ሲሉ ተናግረዋል። የዩኬ ጠቅላይ ሚኒስትር ትራምፕ ኢራን ላይ የወሰዱትን ጥቃት ተችተው የአገራቸውን አቋም ተከላከሉ

  19. የሳተላይት ምስሎች በሳዑዲ የነዳጅ ማጣሪያ ላይ የደረሰ ውድመትን አሳዩ

    የሳዑዲ ነዳጅ ማጣሪያ ላእ ደረሰ ውድመት

    የፎቶው ባለመብት, Vantor

    የምስሉ መግለጫ, በሳዑዲ አረቢያ በሚገኝ የነዳጅ ማጣሪያ ላይ የደረሰ ጉዳትን የሚያሳይ ምስል

    ቢቢሲ ቬርፋይ በሳዑዲ አረቢያ የነዳጅ ማጣሪያ ላይ የድሮን ጥቃት ከተፈጸመ በኋላ የደረሰውን ጉዳት የሚያሳዩ አዳዲስ የሳተላይት ምስሎች ተመልክቷል።

    ቫንቶር ያወጣቸው የሳተላይት ምስሎች በምሥራቅ ራስታኑራ ከተማ በሚገኘው የነዳጅ ማጣሪያ ማዕከላዊ አካባቢ በሚገኙ የማቀዝቀዣ ማማዎች ዙሪያ የእሳት እና የቃጠሎ ምልክቶች ይታያሉ።

    ቦታው የተለያዩ የማከማቻ ክፍሎችን ከጣቢያው ማዕከላዊ ምሰሶ ጋር የሚያገናኙ ተከታታይ ቱቦዎች ያሉት ሲሆን፣ እነዚህም በተለምዶ አራት ታንከሮችን በአንድ ጊዜ መሙላት የሚችሉ ናቸው። ማጣሪያው በቀን 550,000 በርሜል ነዳጅ የማምረት አቅም አለው።

    የአራምኮ የነዳጅ ኩባንያ ባወጣው መግለጫ በጥቃቱ ምክንያት የነዳጅ ማጣሪያው ለጊዜው ተዘግቷል።

    በሳዑዲ አረቢያ በሚገኝ የነዳጅ ማጣሪያ ላይ የደረሰ ጉዳትን የሚያሳይ ምስል

    የፎቶው ባለመብት, Vantor

    የምስሉ መግለጫ, በሳዑዲ አረቢያ በሚገኝ የነዳጅ ማጣሪያ ላይ የደረሰ ጉዳትን የሚያሳይ ምስል
  20. የእስራኤል ጦር በቴህራን እና ቤይሩት ላይ አዲስ ጥቃት መፈጸም ጀመረ

    የእስራአል መከላከያ በኢራን ዋና ከተማ ቴህራን እና የሊባኖስ ዋና ከተማ ቤይሩት ላይ አዲስ ጥቃቶች መፈጸሙን አስታወቀ።

    ጦሩ ባወጣው መግለጫ “በቴህራን እና ቤይሩት የሚገኙ ወታደራዊ ዒላማዎች ላይ ተከታታይ ዒላማቸውን የጠበቁ ጥቃቶች እየፈጸምኩ ነው” ብሏል።

    የእስራኤል ጦር በቤይሩት ጥቃቱን መፈጸም የጀመረው በአገሪቱ ደቡባዊ ክፍል የሚኖሩ ዜጎች አካባቢያቸውን "በአስቸኳይ" ለቅቀው እንዲወጡ ማስጠንቀቂያ ካወጣ በኋላ ነው።

    ጦሩ አክሎም የሔዝቦላህ ማዘዣ ማዕከሎችን እና መሣሪያ ማከማቻ ተቋማትን ዒላማ ማድረጉን ገልጿል።