የአያቶላህ አሊ ኻሜኒን ግድያ ተከትሎ ኢራን እና እስራኤል እንደ አዲስ ጥቃት መፈጸም ቀጥለዋል

የኢራን ጠቅላይ መሪ አያቶላህ አሊ ኻሜኒ በአሜሪካ እና እስራኤል ጥቃት እንደተገደሉ ከተረጋገጠ በኋላ የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ በአሜሪካ የጦር ሰፈሮች እና በእስራኤል ላይ “አስከፊ ጥቃት” እንደሚፈጽም አስጠንቅቋል። ይህንንም ተከትሎ ባህሬን፣ ኩዌት፣ ኳታር፣ የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ኢራቅ እና ኦማን ውስጥ ጥቃት ተፈጽሟል። የእስራኤል ጦርም የኢራን ዋና ከተማ ቴህራንን ዒላማ ያደረጉ ጥቃቶችን መፈጸሙን አስታውቋል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ኢራን እና አሜሪካ አንዳቸው የሌላኛቸውን የጦር መርከብ መምታታቸውን ተናገሩ

    ግዙፉ ዩኤስኤስ አብርሃም ሊንከን የጦር መርከብ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ግዙፉ ዩኤስኤስ አብርሃም ሊንከን የጦር መርከብ

    አሜሪካ የኢራን የጦር መርከብን ማስጠሟን ስትገልጽ፤ ኢራን ደግሞ በግዙፉ የአሜሪካ አውሮፕላን ተሸካሚ መርከብ ላይ በባለስቲክ ሚሳዔሎች ጥቃት መፈጸሟን አስታውቃለች።

    የአሜሪካ ሠራዊት ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንትኮም) በኤክስ ገጹ ላይ እንዳስታወቀው በኢራን ላይ ጥቃት በተጀመረበት ቅዳሜ ዕለት የኢራን የጦር መርከብን መትቶ ማስጠሙን ገልጿል።

    "መርከቡ በኦማን ሰላጤ አካባቢ ባለ የባሕሩ ክፍል ላይ እየሰጠመ ነው” ሲል ሴንትኮም ጨምሮ ገልጿል።

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ደግሞ በባሕረ ሰላጤው ተሰማርቶ በሚገኘው የአሜሪካ የጦር አውሮፕላን ተሸካሚ መርከብ አብርሃም ሊንከን ላይ በአራት ተወንጫፊ ሚሳዔሎች ጥቃት መፈጸሙን የኢራን መንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    ይህንን ተከትሎ የአሜሪካ ሠራዊት ማዕከላዊ ዕዝ የጦር መርከቡ በኢራን ሚሳዔል ተምትቷል መባሉን “የተተኮሱት ሚሳዔሎች አጠገቡም አልደረሱም” በማለት አስተባብሏል።

    ጨምሮም አብርሃም ሊንከን የጦር መርከብ “ከኢራን አገዛዝ ከሚፈጠር ስጋት የአሜሪካ ሕዝብን ለመከላከል በሚካሄደው ያልተቋረጠ ዘመቻ” ላይ የሚሰማሩ አውሮፕላኖችን በማስተናገድ ላይ መሆኑን ገልጿል።

  2. ሦስት የአሜሪካ ወታደሮች መገደላቸውን የአሜሪካ ሠራዊት አስታወቀ

    የአሜሪካ ጦር መርከብ እና የጦር አውሮፕላን

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, አሜሪካ ግዙፍ የጦር መርከቦች፣ የጦር አውሮፕላኖች እና ወታደሮችን በመካከለኛው ምሥራቅ አሰማርታለች

    አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ ጥቃት ከጀመሩበት ከቅዳሜ አንስቶ በግዳጅ ላይ የነበሩ ሦስት የአሜሪካ ወታደሮች መገደላቸውን የሠራዊቱ ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንትኮም) አስታወቀ።

    የወታደሮቹ ሞት ለቤተሰቦቻቸው ተረድቶ 24 ሰዓት እስኪያልፍ ድረስ ስማቸው ይፋ እንደማይሆን ዕዙ ገልጿል።

    የሦስቱ ወታደሮች ሞት በዚህ ዘመቻ የመጀመሪያው በአሜሪካ ወታደሮች ላይ ደረሰ ሞት ነው።

    ከሞቱት በተጨማሪ ሌሎች አምስት ወታደሮች “ክፉኛ መቁሰላቸውን” የአሜሪካ ጦር ሠራዊት ጨምሮ አስታውቋል።

    አሜሪካ ከእስአኤል ጋር በመጣር በኢራን ላይ ጥቃት መክፈቷን ፕሬዝዳንት ትራምፕ ቅዳሜ ዕለት ባሳወቁበት ጊዜ “በጦርነት ውስጥ እንደሚያጋጥመው ጉዳት ሊደርስብን፣ የአሜሪካውያን ጀግኖች ሕይወት ሊጠፋ ይችላል” በማለት አስጠንቅቀው ነበር።

  3. በቅዳሜው ጥቃት የተገደሉ የኢራን ወሳኝ ባለሥልጣናት

    ኤታማዦር ሹሙ አብዶልራሂም ሙሳቪ እና ጠቅላይ መሪው አያቶላህ ኻሜኒ

    የፎቶው ባለመብት, khamenei.ir

    የምስሉ መግለጫ, ኤታማዦር ሹሙ አብዶልራሂም ሙሳቪ እና ጠቅላይ መሪው አያቶላህ ኻሜኒ

    ኢራን ላይ ቅዳሜ ዕለት በተፈጸሙት ጥቃቶች የኢራን መንግሥት ቁልፍ ከፍተኛ ፖለቲካዊ እና ወደታራዊ ባለሥልጣናት ተገድለዋል።

    የአሁኑ ጥቃት ወሳኝ የሚባሉትን የአገሪቱን መሪዎች ዒላማ ያደረገ በመሆኑ የኢራን መንግሥትን ክፉኛ ሊያዳክመው ይችላል እየተባለ ነው።

    ነገር ግን ጠላቶቸቻው አመራሩን ሊመቱ ይችላሉ በሚል ስጋት መሪዎቹ ቀደም ብለው ለእንዲህ ያለው ክስተት መዘጋጀታቸው እየተነገረ ነው።

    ቢሆንም ግን ከአገሪቱ ጠቅላይ መሪ ጀምሮ ከፍተኛ ወደታራዊ መሪዎች የተገደሉበት የኢራን መንግሥት የማይጠገን ጉዳት እንደደረሰበት ይታመናል።

    በጥቃቱ የተገደሉት ቁልፍ ባለሥልጣናት እነ ማን ናቸው?

    • በአገሪቱ መንፈሳዊ፣ ፖለቲካዊ እና ወታደራዊ ጉዳዮች ላይ ዋነኛው ሚና የነበራቸው የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ ጠቅላይ መሪ አያቶላህ አሊ ኻሜኒ በጽህፈት ቤታቸው እንዳሉ ተገደሉ።
    • ኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ መመኪያ የሆነው በአገሪቱ ፖለቲካ፣ ምጣኔ ሀብት እና የውጭ ግንኙነት ውስጥ ሳይቀር ጉልህ ሚና ያለው የአብዮታዊው ዘብ ሠራዊት አዛዥ ጄነራል ሞሐማድ ፓክፑር ተገድለዋል።
    • የኢራን ጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኤታሞዦር ሹም የነበሩት አብዶልራሂም ሙሳቪ ከተገደሉት አንዱ ናቸው።
    • የጠቅላይ መሪው አያቶላ አሊ ኻሜኒ የደኅንነት አማካሪ አሊ ሻምኻኒ ተገድለዋል።
    • የኢራን የመከላከያ ሚኒስትር አዚዝ ናሲርዛዴህ የጥቃቱ ሰለ ባሆነዋል።

    እነዚህ በቁልፍ ቦታዎች ላይ ከፍተኛ ሥልጣን ያላቸው የኢራን መሪዎች ሲሆኑ፣ የደኅንነት እና ወደታራዊ ምንጮች ደግሞ በአጠቃላይ ወደ አርባ የሚደርሱ የኢራን ባለሥልጣናት ተገድለዋል ይላሉ።

  4. ኢራን በኤምሬትስ ላይ በፈጸመችው ጥቃት ኢትዮጵያዊ እና ኤርትራዊ ጉዳት ደረሰባቸው

    ጥቁር ጭስ የሚታይበት ወደብ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, በዱባይ ጀበል አሊ ወደብ ላይ ጥቃት ከተፈጸመ በኋላ

    ኢራን በሁለት ቀናት ውስጥ በተባበሩት አረብ ኤምሬትስ ላይ በፈጸመችው ጥቃት ሦስት ሰዎች ሲገደሉ ኢትዮጵያዊ እና ኤርትራዊን ጨምሮ የተለያዩ አገራት ዜጎች ጉዳት እንደደረሰቸባው ታወቀ።

    የኤምሬትስ የመከላከያ ሚኒስቴር እንዳለው ጥቃቱ ከተጀመረበት ቅዳሜ ዕለት አንስቶ ከሰባት መቶ በላይ ሚሳዔሎች እና ከአምስት መቶ በላይ ድሮኖች ወደ ግዛቱ ከኢራን ተወንጭፏል።

    ከእነዚህም መካከል አብዛኞቹ ሲከሽፉ የተወሰኑት በመኖሪያ እና በሥራ አካባቢዎች እንዲሁም ባሕር ላይ አርፈዋል። በሰው ላይ ጉዳት የደረሰው በቀጥታ በጥቃቶቹ እና ሲከሽፉ በሚፈጠር ስብርባሪ መሆኑ ተገልጿል።

    ገልፍ ኒውስ እንደዘገበው በጥቃቱ ሕይወታቸው የጠፋው ሦስት ሰዎች የፓኪስታን፣ የኔፓል እና የባንግላዲሽ ዜጎች ናቸው። በተጨማሪም ኢትዮጵያዊ እና ኤርትራዊ ያሉበት 58 የተለያዩ አገራትዜጎች ቀላል ጉዳት ደርሶባቸዋል።

    በአሜሪካ እና እስራኤል ጥቃት የተፈጸመባት ኢራን የአሜሪካ የጦር ሰፈር ባለባቸው እና የአሜሪካ ወዳጅ በሆኑ የባሕረ ሰላጤው አገራት ላይ የአጸፋ ጥቃት እየፈጸመች ነው።

  5. በኦማን ባሕር ዳርቻ ላይ የነዳጅ ጫኝ መርከብ ጥቃት ተፈጸመበት

    በኦማን ባሕር ዳርቻ ላይ አንድ ነዳጅ ጫኝ መርከብ ተመትቶ አራት ሰዎች መጎዳታቸውን የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘገቡ።

    ጥቃት የደረሰበት በፓላው ባንዲራ የሚንቀሳቀስ ‘ስካይላይት’ የተባለ የነዳጅ ጫኝ መርከብ እንደሆነ ኦማን ውስጥ የሚገኘው የባሕር ደኅንነት ማዕከል አስታውቋል። ጥቃቱ የተፈጸመው በሰሜናዊ ኦማን ከሚገኘው ካሃሳብ ወደብ አምስት ማይል ርቀት ላይ እንደሆነም ገልጿል።

    ጉዳት የደረሰባቸው አራት የመርከቡ ሠራተኞች ደኅንነታቸው ተጠብቆ እንዲወጡ መደረጉን የኦማን ዜና ወኪል ዘግቧል። ዘገባው እንደሚያሳየው ከመርከቡ ሠራተኞች ውስጥ 15ቱ ሕንዳውያን ቀሪዎቹ አምስት ሰዎች ደግሞ የኢራን ዜጎች ናቸው።

    በሰሜናዊ ኦማን እየተስተዋለ ያለው አጠራጣሪ እንቅስቃሴ በባለሥልጣናት ምርመራ እየተደረገበት መሆኑን የዩናይትድ ኪንግደም ማሪታይም ንግድ ኦፕሬሽን መሥሪያ ቤት ገልጿል።

    ዱቃም የተሰኘው የንግድ ወደብም በሁለት ድሮኖች ዒላማ ተደርጎ እንደነበር የዜና ወኪሉ ዘግቧል። በተንቀሳቃሽ መኖሪያ ላይ ባረፈ የድሮን ጥቃት ምክንያት አንድ ሠራተኛ እንደቆሰለ ተገልጿል። የሁለተኛው ድሮን ስብርባሪ ደግሞ ከነዳጅ ማጠራቀሚያ ታንከር አጠገብ እንደወደቀ የደኅንነት ምንጮች ለኦማን ዜና ወኪል ተናግረዋል።

  6. የኢራን ፕሬዝዳንት፤ የኻሜኒ ግድያ ሁሉም ሙስሊም ላይ “የተከፈተ ጦርነት ነው” አሉ

    የኢራን ፕሬዝዳንት ማዑድ ፔዜሽኪያን

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የኢራን ፕሬዝዳንት ማዑድ ፔዜሽኪያን፤ የአያቶላህ አሊ ኻሜኒ ግድያ “በሁሉም የዓለም ጥግ በሚገኙ ሙስሊሞች፤ በተለይም በሺዓዎች ላይ የተከፈተ ግልጽ ጦርነት” ነው አሉ።

    ፔዜሽኪያን፤ በኢራን መንግሥት ይፋዊ የቴሌግራም ቻናል ላይ በወጣ መግለጫቸው፤ ኢራን “በዚህ ታሪካዊ ወንጀል ፈጻሚዎች እና ጠንሳሾች ላይ የሚፈጸምን ደም መፍሰስ እና በቀልን እንደ ቅቡል ግዴታ እና መብት እንደምትቆጥረው” ተናግረዋል።

    ኢራን፤ ከዚህ ጋር በተያያዘ ያለባትን “ታላቅ ኃላፊነት እና ግዴታ ለመወጣት የተቻላትን ሁሉ እንደምታደርግም” ገልጸዋል።

    በአሜሪካ እና እስራኤል ጥቃት የኢራኑን ጠቅላይ መሪ ጨምሮ ሌሎችም አመራሮች በመገደላቸው ፕሬዝዳንቱ የት እና ምን ዓይነት ሁኔታ ላይ እንደሚገኙ ጥያቄ ሲነሳ ቆይቷል። የፕሬዝዳንቱ ጽሕፈት ቤት ቃል አቀባይ፤ ፔዜሽኪያን “ፍጹም ጤንነት እና ደኅንነት” ላይ እንደሚገኙ ተናግረዋል።

  7. የሔዝቦላህ መሪ፤ የኻሜኒ ግድያ “ትልቅ ወንጀል ነው” ሲሉ አወገዙ

    የሔዝቦላህ መሪ ናይም ቃሲም

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የሔዝቦላህ መሪ ናይም ቃሲም

    የሔዝቦላህ መሪ ናይም ቃሲም፤ የኢራኑ ጠቅላይ መሪ አያቶላህ አሊ ኻሜኒ “በሚሊዮን የሚቆጠሩ ተከታዮችን ጥለው ያለፉ ሰማዕት ናቸው” በማለት በግድያው የተሰማቸውን ሐዘን ገለጹ።

    አያቶላህ አሊ ኻሜኒ ላይ “በወንጀለኞቹ አሜሪካውያን እና በአጥቂዎቹ ፅዮናውያን” የተፈጸመው ግድያ “ትልቅ ወንጀል ነው” ሲሉም አውግዘዋል።

    በሊባኖስ የሚንቀሳቀሰው የሺአ ሙስሊም ቡድን ሔዝቦላህ በኢራን ይደገፋል።

    በመካከለኛው ምሥራቅ ኢራን ድጋፍ ከምትሰጣቸው ቡድኖች በግንባር ቀደምነት የሚጠቀሰው ሔዝቦላህ፤ ለኻሜኒ ያለውን “ታማኝነት” ለማሳየት ሕዝባዊ ሰልፍ ጠርቷል።

  8. የመካከለኛው ምሥራቅ አየር ክልል በመዘጋቱ በረራዎች ተሰረዙ

    እስራኤል እና አሜሪካ ላደረሱት ጥቃት ኢራን የአጸፋ እርምጃ እየወሰደች በምትገኝበት በአሁኑ ወቅት ወደ ቀጣናው የሚደረጉ በረራዎች ተሰርዘዋል።

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    እስራኤል እና አሜሪካ ላደረሱት ጥቃት ኢራን የአጸፋ እርምጃ እየወሰደች በምትገኝበት በአሁኑ ወቅት ወደ ቀጣናው የሚደረጉ በረራዎች ተሰርዘዋል። አንዳንድ በረራዎች ደግሞ ሌላ አማራጭ መንገድ እንዲከተሉ ተደርጓል።

    የዱባይ ዋነኛው ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ እና እንዲሁም ማክቱም አውሮፕላን ማረፊያ አጠቃላይ በረራዎችን ሰርዘዋል።

    በተጨማሪም የዱባይ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ አራት ሠራተኞች መጎዳታቸው ተገልጿል።

    ኤምሬትስ እስከ ነገ ሰኞ ድረስ ከዱባይ የሚነሱ በረራዎችን መሰረዙን አስታውቃለች። ኢቲሀድ ደግሞ መነሻቸውን ከአቡ ዳቢ ያደረጉ በረራዎችን ሰርዟል።

    ሌላኛው አየር መንገድ ብሪትሽ ኤርዌይስ ወደ ቴል አቪቭ እና ባሕሬን የሚደረጉ በረራዎችን እስከ ረቡዕ ድረስ ሰርዟል። ወደ አቡ ዳቢ፣ አማን፣ ዶሃ እና ዱባይ የሚደረጉ ጉዞዎች እንደሚሰረዙም ይፋ አድርጓል።

    ቨርጂን አትላንቲክ፣ ሲንጋፖር ኤርላይንስ፣ ኤር ኢንዲያ እና ሌሎችም አየር መንገዶችም ወደ መካከለኛው ምሥራቅ የሚደረጉ በረራዎችን ሰርዘዋል።

  9. በኢራን በ24 ሰዓታት ውስጥ 57 ሰዎች መገደላቸው ተዘገበ

    ጥቃት የተፈጸመበት ቦታ ላይ የሚታይ ጭስ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ባለፉት በ24 ሰዓታት ኢራን 60 ጥቃቶች እንደተፈጸሙባት እና በእነዚህ ጥቃቶች 57 ሰዎች መገደላቸውን የቴህራን ግዛት የቀይ ጨረቃ ማኅበርን መግለጹን የኢራን መንግሥት የዜና ወኪል ‘ኢርና’ ዘገበ።

    የእስራኤል ጦር ዋና ከተማዋ ቴህራንን ዒላማ ያደረጉ ጥቃቶችን መፈጸሙን ገልጿል። ጦሩ ዒላማ ያደረገው ከኢራን አገዛዝ ጋር ግንኙነት ባላቸውን ሥፍራዎች ላይ እንደሆነ ተናግሯል።

    በከተማዋ ሰማይ ላይ ጭስ ሲወጣ ሚያሳዩ ምሥሎችም ወጥተዋል።

    ቢቢሲ እኩለ ቀን ላይ ያነጋገራቸው የምሥራቃዊ እና ሰሜን ምዕራባዊ ቴህራን ነዋሪዎች በከተማዋ ከፍተኛ ፍንዳታ መሰማቱን ገልጸዋል።

    በምሥራቃዊ ቴህራን የሚገኝ አንድ ምንጭ የዛሬዎቹ “ፍንዳታዎች ከትናንቱ የባሱ” እንደነበሩ ተናግሯል። “ክፍሌ በሙሉ ሲንቀጠቀጥ ነበር” ሲልም ሁኔታውን ገልጿል።

    የኢራን መገናኛ ብዙኃንም በተለያዩ የቴህራን አካባቢዎች ፍንዳታዎች ስለመሰማታቸው ዘግበዋል።

    ጥቃት የተፈጸመበት ቦታ ላይ የሚታይ ጭስ

    የፎቶው ባለመብት, AFP/Getty Images

    ጥቃት የተፈጸመበት ቦታ ላይ የሚታይ ጭስ

    የፎቶው ባለመብት, AFP/Getty Images

  10. ፑቲን፤ የኻሜኒን ግድያ “እኩይ ድርጊት” ሲሉ አወገዙ

    ቭላድሚር ፑቲን

    የፎቶው ባለመብት, Alexander Nemenov/Pool via REUTERS

    የሩሲያው ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን፤ የኢራኑ ጠቅላይ መሪ አያቶላህ አሊ ኻሜኒን ግድያ “እኩይ ድርጊት” እና “ሰብአዊ ሞራልን እንዲሁም ዓለም አቀፍ ሕግን የጣሰ ነው” በማለት ኮነኑ።

    በአያቶላህ አሊ ኻሜኒ ግድያ የተሰማቸውን ሐዘን መግለጻቸውን የሩሲያ መንግሥት የሚያስተዳድረው ታስ ዘግቧል።

    እስራኤል እና አሜሪካ በፈጸሙት የተቀናጀ ጥቃት የኢራኑ ጠቅላይ መሪ መገደላቸውን ተከትሎ በአገሪቱ የ40 ቀን ሐዘን ታውጇል።

    ኢራን የሩሲያ የቅርብ ወዳጅ ሰትሆን፤ ከዓመታት በፊት በምዕራባውያን አገራት በተፈረመው የኒውክሌር ስምምነት ውስጥ ከሚገኙ አገራት አንዷ ሩሲያ ነበረች።

  11. የባሕረ ሰላጤው አገራት የኢራንን ጥቃት “እየመከቱ” እንደሆነ ገለጹ

    ኢራን ጥቃት ከፈጸመች በኋላ ከዱባይ የባሕር ዳርቻ ላይ ጥቅጥቅ ያለ ጭስ ሲወጣ ታይቷል

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ኢራን ጥቃት ከፈጸመች በኋላ ከዱባይ የባሕር ዳርቻ ላይ ጥቅጥቅ ያለ ጭስ ሲወጣ ታይቷል

    ኢራን የአጸፋ ምላሽ ዒላማ ያደረገቻቸው የባሕረ ሰላጤው አገራት የተሰነዘረባቸውን ጥቃት “እየመከቱ” እንደሚገኙ አስታውቀዋል።

    ባሕሬን የተተኮሱባትን ባለስቲክ ሚሳዔሎች በአየር መቃወሚያዋ አማካኝነት ማክሸፏን ገልጻለች። ሆኖም የተወሰኑ “ስብርባሪዎች” በአንዳንድ የአገሪቱ ክፍል መውደቃቸውን የአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    ኩዌት “የተቃጡብኝን አደገኛ የአየር ጥቃቶች መከላከል ችያለሁ” ስትል በመከላከያ ሚኒስቴሯ በኩል አስታውቃለች። በሰሜናዊ የአገሪቱ ክፈል የተሰነዘሩ ጥቃቶችን በማምከኗ ሰዎች እንዳልተጎዱ የአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ዘገባ ያሳያል።

    ኳታር በበኩሏ የተሰነዘረባት የሰው አልባ አውሮፕላን ጥቃት በተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ቢከሽፍም አንዲት ሴት እና ልጇ መጎዳታቸውን ይፋ አድርጋለች። በአቡ ዳቢ የሚገኘው ‘ዩኒየን ታወር’ ጉዳት እንደደረሰበት ተገልጿል።

    የኳታር መከላከያ እንዳለው ከኢራን የተወነጨፉ ሚሳዔሎች እና ተዋጊ ጀቶችን “በተሳካ ሁኔታ” ማምከን ተችሏል።

  12. በኢራን የሚሳዔል ጥቃት ሁለት እስራኤላውያን መገደላቸው ተገለጸ

    የእስራኤል መከላከለያ ቃል አቀባይ ኤፊ ደርፊን

    የፎቶው ባለመብት, IDF

    የምስሉ መግለጫ, የእስራኤል መከላከለያ ቃል አቀባይ ኤፊ ደርፊን

    ኢራን በፈጸመችው የአጸፋ የሚሳዔል ጥቃት ሁለት እስራኤላውያን መገደላቸው ተገለጸ። የእስራኤል መከላከለያ ቃል አቀባይ ኤፊ ደርፊን “የአየር መቃወሚያ መሣሪያችን ጠንካራ ቢሆንም ፍጹም አይደለም” ብለዋል።

    እስራኤላውያን የሚተላለፍላቸውን ትዕዛዝ ተከትለው ከምድር በታች በሚገኙ መጠለያዎች እንዲቆዩ አሳስበዋል።

    የኢራንን መከላከያ “ክፉኛ እንደጎዱ” የተናገሩት ቃል አቀባዩ፤ ከአሜሪካ ጋር የከፈቱት የተቀናጀ ጥቃት እንደሚቀጥል አስታውቀዋል።

    ሁለቱ አገራት ኢራን ላይ ጥቃት ከከፈቱ በኋላ 456 ሰዎች ተጎድተው ሆስፒታል እንደገቡ እና 86 የሚሆኑት በጽኑ ሕሙማን ክፍል እንደሚገኙ ቃል አቀባዩ ገልጸዋል።

  13. በእስራኤል ጥቃት 30 ከፍተኛ የኢራን ባለሥልጣናት መገደላቸው እየተነገረ ነው

    ቴህራን ውስጥ ጥቃት የደረሰበት ተሽከርካሪ

    የፎቶው ባለመብት, ISNA/WANA/Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ቴህራን ውስጥ ጥቃት የደረሰበት ተሽከርካሪ

    የእስራኤል አየር ኃይል ቅዳሜ ዕለት ኢራን ላይ በፈጸመው ጥቃት ጠቅላይ መሪው አያቶላህ አሊ ኻሜኒን ጨምሮ በአጠቃላይ 30 የአገሪቱን ከፍተኛ ባለሥልጣናት መግደሉ ተነገረ።

    ቻናል 12 የተባለው የእስራኤል ቴሌቪዥን እንደዘገበው ዒላማ የተደረጉት መሪዎች የተገደሉት “ጥቃቱ በተጀመረ በመጀመሪያው ግማሽ ደቂቃ” ላይ መሆኑን አመልክቷል።

    ጨምሮም የእስራኤል የፖለቲካ እና የደኅንነት ባለሥልጣናት ኢራን ላይ የተከፈተው ጥቃት “ጅማሬ እንደሆነ እና ዘመቻው ለቀጣይ በርካታ ቀናት እንደሚቀጥል” መናገራቸውን ዘግቧል።

    ሌሎች የእስራኤል መገናኛ ብዙኃን ደግሞ የአሜሪካ እና እስራኤል ጦር ሠራዊቶች በኢራን ላይ የፈጸሙት በመጠነ ሰፊ ዕቅድ እና ጠንካራ ትበብር እንደነበረ እና ትክክለኛ መረጃ እንደነበራቸው ጠቅሷል።

    በኢራን ላይ የተፈጸመውን ጥቃት ተከትሎ የተባበሩት መንግሥታት እና አገራት ተቃውሟቸውን እያሰሙ ነው። የእስራኤል ባለሥልጣናት እንደሚፈልጉት አሜሪካ ዘመቻውን ለረዥም ጊዜ የማካሄድ ፍላጉት ላይኖራት እንደሚችል የመከላከያ ተንታኙ ዮአቭ ሊሞር ተናግረዋል።

    በጥቃቱ ከምክር ቤት አባላት እና ከአሜሪካውያን ተቃውሞ እየቀረበባቸው ያሉት ትራምፕ ኢራን ውስጥ የሚፈልጉት የሥርዓት ለውጥ እስኪመጣ ላይቀጥሉ ይችለሉ።

  14. የኢራን አብዮታዊ ዘብ አዲስ አዛዥ ተሾመለት

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    አህመድ ቫሂዲ የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ አዲስ ዋና አዛዥ ሆነው ተሾሙ።

    ወታደራዊ ኃይሉን ሲመሩ የነበሩት ጄነራል መሐመድ ፓክፑር እስራኤል እና አሜሪካ ቅዳሜ ዕለት ኢራን ላይ በፈጸሙት ጥቃት ተገድለዋል።

    አብዮታዊ ዘቡ ኢራን ውስጥ ወታደራዊ፣ ፖለሪካዊ እና ኢኮኖሚያዊ ኃይሎችን የሚያንቀሳቅስ ዋና ኃይል ሲሆን የተዋቀረውን ከአገሪቱ መደበኛ ጦር ተነጥሎ ነው።

    አሜሪካ እና እስራኤል በፈጸሙት ጥቃት በርካታ የኢራን ከፍተኛ ወታደራዊ አዛዦች መገደላቸውን ተከትሎ፤ በአሁኑ ሰዓት የኢራንን ወታደራዊ ኃይል በማን እየተመራ ነው የሚለው እያነጋገረ ነው።

    በኢራን መገናኛ ብዙኃን ዘገባዎች መሠረት ሜጀር ጄኔራል አሊ አብዶላሂ ወታደራዊ ኃይሉን እየመሩ ይመስላል።

    ሜጀር ጄነራሉ፤ በኢራን ጦር እና በአብዮታዊ ዘቡ መካከል ሆኖ የአገሪቱን መከላከያ ሠራዊት የሚያስተባብረው የኻተም አል አንቢያ ማዕከላዊ ዋና መሥሪያ ቤት አዛዥ ናቸው።

    ሜጀር ጄነራሉ፤ ኢራን “ለጠላቶች ዛቻ ምላሽ የምትሰጠው በጦር ግንባር” ነው ብለዋል። “ጦር ኃይሎቹ ዝግጁነት ከመቼውም በላይ ከፍተኛ ደረጃ ላይ እንደሚገኝም” ተናግረዋል።

    አብዶላሂ፤ ኢራን ኢራቅ ውስጥ የሚኝ የአሜሪካ ጦር ሰፈሮች ላይ የሚሳዔል ጥቃት መፈጸሟን ተከትሎ በዋሽንግተን ማዕቀብ ከተጣለባቸው ወታደራዊ አዛዦች አንዱ ናቸው።

  15. ፓኪስታን ውስጥ ኢራንን በመደገፍ የአሜሪካ ቆንስላ አቅራቢያ ሰልፍ ከወጡ ሰዎች ቢያንስ ዘጠኙ ሞቱ

    የፓኪስታን ሰልፈኞች

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በፓኪስታን ካራቺ ከተማ ውስጥ የሚገኘው የአሜሪካ ዋና ቆንስላ አቅራቢያ ተቃውሟቸውን ያሰሙ ሰልፈኞች ከፖሊስ ጋር ተጋጭተው ቢያንስ ዘጠኝ ሰዎች እንደሞቱ እና 32 እንደቆሰሉ ተነገረ።

    ቢቢሲ ያነጋገራቸው በካራቺ የሚገኝ የሲቪል ሆስፒታል ከፍተኛ ሐኪም የዘጠኝ ሰዎች አስከሬን ወደ ሕክምና ተቋሙ እንደተወሰደ ገልጸዋል።

    አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ የፈጸሙትን ጥቃት ተከትሎ በመቶዎች የሚቆጠሩ የቴህራን ደጋፊዎች በካራቺ፣ ላሆር እና ኢስላማባድ ከተሞች ወደ ጎዳና በመውጣት ተቃውሟቸውን አሰምተዋል።

    ኤድሂ ፋውንዴሽን’ የተባለው የግል የነፍስ አድን ተቋም አንድ ኃላፊ፤ ዘጠኝ አስክሬን እና በርካታ የቆሰሉ ሰዎችን ወደ ሆስፒታል መውሰዳቸውን አረጋግጠዋል።

    ግጭቱ የተጀመረው ፖሊስ ተቃዋሚዎች ወደ አሜሪካ ቆንስላ ግቢ እንዳይገቡ በተከላከሉበት ወቅት ነው። ክስተቱን በተመለከተ እስካሁን ፖሊስ ይፋዊ መግለጫ አልሰጠም።

    ጊልጊት ከተማ ውስጥ ደግሞ አንድ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ቢሮ መቃጠሉን አንድ የድርጅቱ ባለሥልጣን ለቢቢሲ ኒውስ ተናግረዋል።

    በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ወደ ጎዳና የወጡበትን ተቃውሞ ተከትሎ በአካባቢው የሰዓት እላፊ እንደታወጀ ፖሊስ አረጋግጧል።

    የአገሪቱ የሺዓ ድርጅቶች፤ ዋና ከተማዋ ኢስላማባድን ጨምሮ በበርካታ አካባቢዎች የተቃውሞ ሰልፎች ጠርተዋል።

  16. ኢራናውያን በመሪያቸው ሞት ሐዘናቸውን ለመግለጽ አደባባይ ወጡ

    አደባባይ የወጡ ኢራናውያን

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, በመሪያቸው ሞት ሐዘናቸውን ለመግለጽ አደባባይ የወጡ ኢራናውያን

    አራት አስርት ዓመታት ለሚጠጋ ጊዜ ኢራንን በጠቅላይ መሪነት ያስተዳደሩት አያቶላህ አሊ ኻሜኒ መገደልን ተከትሎ ዜጎች አደባባይ ወጥተው ሐዘናቸውን እየገለጹ ነው።

    እስራኤል እና አሜሪካ በፈጸሙት ጥቃት ከቅርብ የቤተሰብ አባሎቻቸው እና ከፍተኛ የአገሪቱ ባለሥልጣናት ጋር የተገደሉት ጠቅላይ መሪው ሞት ኢራናውያንን ለሁለት ከፍሏል።

    በአገር ውስጥ እና በውጪ ያሉ የአገሪቱ ዜጎች በመሪው ኅልፈት ሐዘናቸውን እና ደስታቸውን ሲገልጹ መታየታቸው ተዘግቧል።

    ለእስላማዊው የኢራን ሪፐብሊክ መንግሥት ከባድ ጉዳት ለሆነው የኻሜኒ ሞት ከአንድ ወር በላይ የሚቆይ የሐዘን ጊዜ ታውጇል።

    የአገሪቱ ቴሌቪዥን አቅራቢ በከባድ ሐዘን እንባ እየተናነቀው የመሪው ሞት ካወጀ በኋላ በዋና ከተማዋ ቴህራን ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ኢራናውያን ሐዘናቸውን ለመግለጽ አደባባይ ወጥተዋል።

  17. የኢራን ጄቶች በመካከለኛው ምሥራቅ የሚገኙ የአሜሪካ የጦር ሰፈሮችን መደብደባቸው ተዘገበ

    ከኢራን የሚሳዔል ጥቃት በኋላ ዶሃ ውስጥ ጭስ ታይቷል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ከኢራን የሚሳዔል ጥቃት በኋላ ዶሃ ውስጥ ጭስ ታይቷል

    የኢራን የአየር ኃይል አብራሪዎች በባሕረ ሰላጤው አገራት እና በኢራቅ ኩርዲስታን ግዛት የሚገኙ የአሜሪካ የጦር ሰፈሮች ላይ በተሳካ ሁኔታ ድብደባ መፈጸማቸውን የአገሪቱ መንግሥት የዜና ወኪል የሆነው ‘ኢርና’ ዘገበ።

    የኢራን ጦር፤ ጄት አብራሪዎቹ በጦር ሰፈሮቹ ላይ የተሳካ ጥቃት የፈጸሙት በተለያዩ ምዕራፎች እንደሆነ ገልጿል። ሁሉም በቀጣናው የሚገኙ “የጠላት ወታደራዊ ማዕከላት” በአየር ኃይሉ ተዋጊ ጄቶች የመድረስ አቅም ሥር እንደሚገኙም አክሏል።

    በተያያዘ ዜና ኢራን በባሕረ ሰላጤው በሚገኙ የአሜሪካ አጋር አገራት ላይ የፈጸመችውን ጥቃት ተከትሎ በከተሞቹ ጭስ እና እሳት ታይቷል። ይህንን ሁኔታ የሚያሳዩ ምሥሎችም መውጣት ጀምረዋል።

    ትናንት ሌሊት እና ዛሬ ጠዋት የተነሱት እነዚህ ምሥሎች፤ በባህሬን ዋና ከተማ ማናማ እና በተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ጀበል አሊ ወደብ የተከሰተውን እሳት ያሳያሉ።

    በባህሬን ዋና ከተማ ማናማ ውስጥ በኢራን ድሮን ተመትቶ ከሚቃጠል ህንጻ ላይ ጭስ ሲወጣ ታይቷል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, በባህሬን ዋና ከተማ ማናማ ውስጥ በኢራን ድሮን ተመትቶ ከሚቃጠል ህንጻ ላይ ጭስ ሲወጣ ታይቷል
    የኢራን ጥቃት ከደረሰበት የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ጀበል አሊ ወደብ ጥቁር ጭስ ወደላይ ሲጎን ተስተውሏል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የኢራን ጥቃት ከደረሰበት የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ጀበል አሊ ወደብ ጥቁር ጭስ ወደላይ ሲጎን ተስተውሏል
  18. ኢራን የአጸፋ ጥቃት መፈጸም መጀመሯን ተከትሎ ዶሃ ውስጥ ፍንዳታዎች ተሰሙ

    በኢራን ጥቃት የተመታው የዱባይ ጄበል አሊ ወደብ ላይ እሑድ ጠዋት ጭስ ታይቷል

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, በኢራን ጥቃት የተመታው የዱባይ ጄበል አሊ ወደብ ላይ እሑድ ጠዋት ጭስ ታይቷል

    በመካከለኛው መሥራቅ የሚገኙ የአሜሪካ የጦር ሰፈሮችን ዒላማ እያደረገች ያለችው ኢራን፤ በባሕረ ሰላጤው አገራት ላይ የምትፈጽመውን ጥቃት በድጋሚ ጀምራለች።

    ዛሬ ጠዋት በኳታር ዋና ከተማ ዶሃ ውስጥ ከፍተኛ ፍንዳታ ተሰምቷል፤ በከተማዋ ሰማይ ላይም ወደላይ የሚጎን ጭስ ታይቷል።

    የኳታር የአገር ውስጥ ደኅንነት ሚኒስቴር፤ እንዲከሽፍ በተደረገ ሚሳዔል ስብርባሪ ምክንያት በከተማዋ በሚገኝ የኢንዱስትሪ ዞን ውስጥ የተከሰተውን መጠነኛ የእሳት አደጋ ለመቆጣጠር እየሠራ መሆኑን አስታውቋል።

    የኳታር ባለሥልጣናት ሌሊት ላይ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፣ ኢራን ትናንት ብቻ 65 ሚሳዔሎችን እና 12 ድሮኖችን ማስወንጨፏን ተናግረዋል።

    አብዛኛዎቹ ተወንጫፊዎች እንዲከሽፉ ቢደረጉም ጉዳት ያደረሱ መኖራቸውን ገልጸዋል። በወደቁ ስብርባሪዎች ምክንያት ስምንት ሰዎች እንደተጎዱም አክለዋል።

    በተጨማሪም ዛሬ ጠዋት በዱባይ እና በባሕሬን ዋና ከተማ ማናማ ፍንዳታዎች ተሰምተዋል። በኦማን የንግድ ወደብ ላይ የድሮን ጥቃት እንደተፈጸመ የአገሪቱ መንግሥት የዜና ወኪል ዘግቧል።

    አሜሪካ እና ኢራንን ለማስታረቅ በሚደረገው ድርድር ለዓመታት ቁልፍ አሸማጋይ የነበረችው ኦማን እስካሁን ድረስ ከኢራን ጥቃቶች ተርፋ ነበር።

    ኳታር እና ሌሎች የተወሰኑ የአረብ አገራት፤ የኢራንን ጥቃት በጽኑ አውግዘዋል። ለተፈጸመባቸው ጥቃት ምላሽ የመስጠት መብት እንዳላቸውም አስታውቀዋል።

    የባሕረ ሰላጤው አገራት ባለፉት ዓመታት ከኢራን ጋር ያላቸውን ውጥረት ለማርገብ ጥረት ሲያደርጉ ቆይተዋል።

    ከአሜሪካ ጋር ለገባችበት ቀውስ ዲፕሎማሲያዊ መፍትሔ ለማበጀትም በአሸማጋይነት ሲሠሩ የሰነበቱት እነዚህ አገራት፤ ኢራን በግዛታቸው ውስጥ በሚገኙ የአሜሪካ የጦር ሰፈሮች ላይ ጥቃት እንዳትፈጽም ሲከለክሉ ነበር።

    ይህ ማሳሰቢያቸው ግን ግዛታቸው ውስጥ ቀጥታ ጥቃት እንዳይፈጸም ሊያደርግ አልቻለም። አሁን ደግሞ የኢራን ጠቅላይ መሪ በተፈጸመው ጥቃት መገደላቸውን ተከትሎ ከቴህራን በተጨማሪ የመላው ቀጣናው መጻኢ ሁኔታ ምን ሊመስል እንደሚችል በእርግጠኝነት መናገር አዳጋች ሆኗል።

  19. የኢራን ጠቅላይ መሪ አያቶላህ አሊ ኻሜኒ ማን ነበሩ?

    ኻሜኒ

    የፎቶው ባለመብት, leader.ir

    እስራኤል "ከምድረ ገጽ እንድጠፋ ይፈልጋሉ" ስትል የምትከሳቸውን ኻሜኒን ለማጥመድ ለአስርታት ስታደባ ቆይታለች።

    ጠቅላይ መሪውን ግን በቀላሉ ዒላማ ሳይሆኑ ቆይተው ቅዳሜ የካቲት 21/2018 ጽህፈት ቤታቸው ላይ በተፈጸመ ከባድ ጥቃት መገደላቸው ተረጋግጧል።

    የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ ጠቅላይ መሪ የነበሩት የ86 ዓመቱ አዛውንቱ መሪ ማን ነበሩ? በኢራን አብዮት እና በጠቅላይ መሪነቱ ውስጥ ምን ሚና ነበራቸው? ከየትስ ተነስተው የኢራን ጠቅላይ መሪነት ላይ ደረሱ?

  20. የአፍሪካ መሪዎች፤ የኢራን ጦርነት ዓለም አቀፋዊ እና ቀጣናዊ መረጋጋትን ሊያናጋ እንደሚችል አስጠነቀቁ

    የደቡብ አፍሪካ ፕሬዝዳንት ሲሪል ራማፎሳ እና የኬንያ ፕሬዝዳንት ዊልያም ሩቶ

    የፎቶው ባለመብት, EPA/State House Kenya

    የምስሉ መግለጫ, የደቡብ አፍሪካ ፕሬዝዳንት ሲሪል ራማፎሳ እና የኬንያ ፕሬዝዳንት ዊልያም ሩቶ

    የአፍሪካ አገራት መሪዎች በአሜሪካ፣ እስራኤል እና ኢራን ግጭት ምክንያት በመካከለኛው ምሥራቅ እየተባባሰ የመጣው ውጥረት የዓለምን ደኅንነት ሊያናጋ እና ለአፍሪካ ከፍተኛ ኢኮኖሚያዊ ጉዳት ሊያመጣ እንደሚችል አስጠነቀቁ።

    የደቡብ አፍሪካ ፕሬዝዳንት ሲሪል ራማፎሳ ሁሉም ወገኖች በከፍተኛ መጠን እንዲታቀቡ እና ወደ ዲፕሎማሲ እንዲመለሱ አሳስበዋል። እየጨመረ የመጣው ውጥረት በዓለም አቀፍ ሰላም እና ደኅንነት ላይ ከፍተኛ ስጋት መደቀኑንም በማንሳት አስጠንቅቀዋል።

    የደቡብ አፍሪካን ታሪክ ለአብነት የጠቀሱት ራማፎሳ፤ ዘላቂ ሰላም ሊሳካ የሚችለው በንግግር፣ በፍትሕ እና አብሮ በመኖር ብቻ እንደሆነ ተናግረዋል።

    አገርነቷን ያወጀችው ሶማሊላንድ እና በግዛቷ የሚገኙ የተቃዋሚ ፓርቲዎች በበኩላቸው ኢራን በባሕረ ሰላጤው የፈጸመችውን ጥቃት በማንሳት ወቅሰዋል። የኢራን ጥቃት ቀጣናዊ መረጋጋትን አደጋ ላይ እንደሚጥለውም አስጠንቅቀዋል።

    ሱዳንም በተመሳሳይ ኳታር፣ ኩዌት፣ ዮርዳኖስ እና ባሕሬን ላይ የተፈጸመውን የኢራን የሚሳዔል ጥቃት የሚያወግዝ ጠንካራ መግለጫ ማውጣቷን በአገሪቱ የሚገኘው የዜና ምንጭ ‘ሱዳን ትሪቡን’ ዘግቧል። በኻርቱም መግለጫ ላይ ጥቃት የተፈጸመባት ሌላኛዋ የባሕረ ሰላጤው አገር የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ሳትጠቀስ ቀርታለች።

    በተባበሩት መንግሥታት የሚገኘው የአፍሪካ ኅብረት ተልዕኮ በበኩሉ፤ አሜሪካ እና እስራኤል ኢራን ላይ የፈጸሙትንም፤ የቴህራንንም የአጸፋ ምላሽ ተችቷል። ግጭቱ ይበልጥ እንዳይባባስ ለመከላከል ሲባል በተባበሩት መንግሥታት በኩል እንደ አዲስ ዲፕሎማሲያዊ ጥረት እንዲደረግም አሳስቧል።

    በርካታ የአፍሪካ አገራት በቀውሱ የተጠለፉ ዜጎቻቸውን ደኅንነት ለማስጠበቅ የተለያዩ እርምጃዎችን ወስደዋል። ኡጋንዳ፤ ኢራን ውስጥ የሚገኙ ዜጎቿ የሚቻል ከሆነ ለቅቀው እንዲወጡ አሳስባለች። በቴህራን በሚገኘው ኤምባሲ ውስጥ የሚገኙ ወሳኝ ያልሆኑ ሠራተኞችንም አስወጥታለች።

    ኬንያ ደግሞ በመካከለኛው ምሥራቅ የተፈጠረው አለመረጋጋት፤ በቀጣናው በሚገኙ መስመሮች አማካኝነት ወደተለያዩ አገራት የሚደርሱትን እንደ ሻይ፣ ቡና፣ አበባ፣ ሥጋ እና አትክልት ያሉ ዋና ዋና የወጪ ንግድ ምርቶችን ለመላክ እንቅፋት እንደሚሆን ተናግራለች።

    ከባሕረ ሰላጤው አገራት ጋር ጠንካራ የንግድ ትስስር ያላቸው ኬንያ እና ታንዛኒያ፤ የመርከብ መስመሮች ለተራዘመ ጊዜ የሚዘጉ ከሆነ በወጪ ንግድ ገቢያቸው ላይ ሊደርስ ስለሚችለው ጉዳት ስጋታቸውን ገልጸዋል።