ኢራን እና አሜሪካ አንዳቸው የሌላኛቸውን የጦር መርከብ መምታታቸውን ተናገሩ

የፎቶው ባለመብት, Reuters
አሜሪካ የኢራን የጦር መርከብን ማስጠሟን ስትገልጽ፤ ኢራን ደግሞ በግዙፉ የአሜሪካ አውሮፕላን ተሸካሚ መርከብ ላይ በባለስቲክ ሚሳዔሎች ጥቃት መፈጸሟን አስታውቃለች።
የአሜሪካ ሠራዊት ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንትኮም) በኤክስ ገጹ ላይ እንዳስታወቀው በኢራን ላይ ጥቃት በተጀመረበት ቅዳሜ ዕለት የኢራን የጦር መርከብን መትቶ ማስጠሙን ገልጿል።
"መርከቡ በኦማን ሰላጤ አካባቢ ባለ የባሕሩ ክፍል ላይ እየሰጠመ ነው” ሲል ሴንትኮም ጨምሮ ገልጿል።
የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ደግሞ በባሕረ ሰላጤው ተሰማርቶ በሚገኘው የአሜሪካ የጦር አውሮፕላን ተሸካሚ መርከብ አብርሃም ሊንከን ላይ በአራት ተወንጫፊ ሚሳዔሎች ጥቃት መፈጸሙን የኢራን መንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።
ይህንን ተከትሎ የአሜሪካ ሠራዊት ማዕከላዊ ዕዝ የጦር መርከቡ በኢራን ሚሳዔል ተምትቷል መባሉን “የተተኮሱት ሚሳዔሎች አጠገቡም አልደረሱም” በማለት አስተባብሏል።
ጨምሮም አብርሃም ሊንከን የጦር መርከብ “ከኢራን አገዛዝ ከሚፈጠር ስጋት የአሜሪካ ሕዝብን ለመከላከል በሚካሄደው ያልተቋረጠ ዘመቻ” ላይ የሚሰማሩ አውሮፕላኖችን በማስተናገድ ላይ መሆኑን ገልጿል።






















