የእስራኤል እና ኢራን ግጭት “መስፋፋት ማንም ሊቆጣጠረው የማይችል እሳት ሊያቀጣጥል ይችላል” ተመድ

ስምንተኛ ቀኑን የያዘው የእስራኤል እና ኢራን ግጭት “መስፋፋት ማንም ሊቆጣጠረው የማይችል እሳት ሊያቀጣጥል ይችላል” ሲሉ የተባበሩት መንግሥታት ዋና ጸሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ አሳሰቡ።ዋና ጸሐፊው በአገራቱ መካከል ያለው ግጭት መቀጠል አለምን ወደ ቀውስ የሚከት ነው ብለዋል።

ጭምቅ ሃሳብ

  • እስራኤል እና ኢራን ግጭት "መስፋፋት ማንም ሊቆጣጠረው የማይችል እሳት ሊያቀጣጥል ይችላል" ሲሉ የተባበሩት መንግሥታት ዋና ጸሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ አሳሰቡ
  • ኢራን በእስራኤል ያልተጠበቀ ጥቃት የተፈጸመባት "ከአሜሪካ ጋር የኒውክሌር አቅምን አስመልክቶ ተስፋ ሰጪ ዲፕሎማሲያዊ ሂደት ላይ በነበረችበት ወቅት" መሆኑን አስታወቀች።
  • የፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት ኢማኑኤል ማክሮን ከእስራኤል ጋር ያለውን ግጭት ለማስቆም ፈረንሳይን ጨምሮ አውሮፓውያኑ አገራት ለኢራን የዲፕሎማሲ ፕሮፖዛል እንደሚያቀርቡ ተናግረዋል።
  • ዶናልድ ትራምፕ በሚቀጥሉት ሁለት ሳምንታት ውስጥ ዩናይትድ ስቴትስ በኢራን እና በእስራኤል ግጭት ውስጥ በቀጥታ ጣልቃ መግባት አለመግባቷን ይወስናሉ- ዋይት ሐውስ
  • ትራምፕ በመካከለኛው ምሥራቅ ግጭት ላይ ለመወሰን ሁለት ሳምንት ጊዜ ሲሰጡ ዩኬ እና የአውሮፓ ኅብረት ከኢራን ጋር ሊነጋገሩ ነው
  • የኢራን ውጪ ጉዳይ ሚኒስትር ለቢቢሲ አሜሪካ በግጭቱ ውስጥ የምትሳተፍ ከሆነ ቀጠናው "ሲኦል" ይሆናል ሲሉ ተናግረው ነበር
  • ኢራን በትናንትናው ዕለት በፈጸመችው የሚሳኤል ጥቃት ከሆስፒታል አቅራቢያ ያለ ወታደራዊ ስፍራ ማነጣጠሩን ገልጽላች
  • ኢራን ባስወነጨፈቻቸው ሚሳኤሎች በደቡባዊ እስራኤል ባርሺባ ከተማ የሚገኘውና በእስራኤል ትልቁ ከሚባሉት አንዱ ሶሮካ ሆስፒታል መመታቱን እስራኤል አስታወቀች።
  • የተመድ የጸጥታው ምክር ቤት በእስራኤል እና ኢራን ግጭት አስቸኳይ ስብሰባ ሊያካሂድ ነው
  • የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ኢራንን ለማጥቃት ዕቅድ ቢያጸድቁም ነገር ግን የመጨረሻ ውሳኔ ላይ አለመድረሳቸው ተዘገበ።
  • አሜሪካ የጦር ጄቶችን ጨምሮ የጦር መሳሪያዎችን ወደ መካከለኛው ምስራቅ እያንቀሳቀሰች ነው
  • ፑቲን በኻሜኒ ላይ የታቀደውን ግድያ አስመልክቶ "በፍጹም በዚህ ጉዳይ ላይ መወያየት አልፈልግም" አሉ
  • የኢራን ጠቅላይ መሪ አያቶላህ አሊ ኻሜኒ "ኢራናውያን እጃቸውን የሚሰጡ ሕዝቦች አይደለም" ሲሉ ተናገሩ።
  • እስራኤል በኢራን ላይ በፈጸመችው ጥቃት እስከ እሁድ ምሽት ድረስ 224 ሰዎች ሲገደሉ 1 ሺህ 277 መጎዳታቸውን ኢራን አስታውቃለች። እስራኤል በበኩሏ በጥቃቶቹ 20 ሰዎች ተገድለውብኛል ብላለች።
  • ትራምፕ ኢራን ላይ ጥቃት መፈጸምን በተመለከተ "ላደርገው ወይም ላላደርገው እችላለሁ" አሉ
  • ፎርዶ ኢራን ካሏት ሁለት ወሳኝ የኒውክሌር ማብላያ ጣቢያዎች መካከል አንዱ ሲሆን የእስራኤል መከላከያ ኃይል የአየር ጥቃት ቢያደርስበትም ጉዳት ሊደርስበት አልቻለም።

የቀጥታ ሽፋን

  1. ኢራን በዛሬው ዕለት በሰሜናዊ እስራኤል ባስወነጨፈቻቸው ሚሳኤሎች በርካቶች መጎዳታቸው ተነገረ

    በእስራኤል ላይ የደረሰው ጥቃት

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ኢራን በዛሬው ዕለት በሰሜናዊ እስራኤል ባስወነጨፈቻቸው ሚሳኤሎች በርካቶች መጎዳታቸውን የአገሪቱ የአደጋ ጊዜ አገልግሎት አስታወቀ።

    የ40 ዓመት ወንድ፣ የ16 ዓመት ወንድ እና የ54 ዓመት ግለሰብ በጠና መቁሰላቸውን የእስራኤል የአደጋ ጊዜ አገልግሎት ማገን ዴቪድ አዶም ገልጿል።

    ሌሎች 20 የሚሆኑት ደግሞ በመለስተኛ ሁኔታ ላይ መሆናቸውን እና ብዙዎቹም በፍንዳታ እና በፍንጣሪዎች ቆስለዋል ብሏል።

    በካርሚኤል መጠለያ የነበረች አንዲት የ51 ዓመት ግለሰብ በልብ ድካም ህይወቷ ማለፉ ተገልጿል።

  2. ዩኬ የኤምባሲ ሰራተኞቿን ከኢራን ልታስወጣ መሆኑን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታወቀ

    የኢራን ከተማ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ዩናይትድ ኪንግደም በኢራን ባለው የጸጥታ ሁኔታ በቴህራን የሚገኙ የኤምባሲ ሰራተኞቿን ልታስወጣ መሆኑን የዩኬ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታወቀ።

    “ሰራተኞቻችንን በጊዜያዊነት ከኢራን ለማስወጣት የጥንቃቄ እርምጃ ወስደናል” ሲል የዩናይትድ ኪንግደም የውጭ፣ የኮመንዌልዝ እና ዴቨሎፕመንት ጽህፈት ቤት በመግለጫው አስታውቋል።

    ሆኖም ኤምባሲው ስራውን እንደማያቆምና “አገልግሎቱን በርቀት እንደሚሰጥ” ገልጿል።

    በሳምንቱ መጀመሪያ በተመሳሳይ መልኩ በደህንንት ስጋት ምክንያት በእስራኤል የሚገኘውን ኤምባሲዋን እና የቆንስላ ሰራተኞቿን ለጊዜው እንደምታስወጣ አስታውቃለች።

  3. የእስራኤል እና ኢራን ግጭት “መስፋፋት ማንም ሊቆጣጠረው የማይችል እሳት ሊያቀጣጥል ይችላል” ተመድ

    አንቶኒዮ ጉቴሬዝ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ስምንተኛ ቀኑን የያዘው የእስራኤል እና ኢራን ግጭት “መስፋፋት ማንም ሊቆጣጠረው የማይችል እሳት ሊያቀጣጥል ይችላል” ሲሉ የተባበሩት መንግሥታት ዋና ጸሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ አሳሰቡ።

    ዋና ጸሐፊው ኒውዮርክ በሚደረገው በተባበሩት መንግሥታት የጸጥታው ምክር ቤት መክፈቻ ንግግራቸው በአገራቱ መካከል ያለው ግጭት መቀጠል አለምን ወደ ቀውስ የሚከት ነው ብለዋል።

    ጉቴሬዝ የግጭቱ ማዕከል “የኒውክሌር ጥያቄ” ነው ብለው እንደሚያምኑ ተናግረዋል።

    “ኢራን የኒውክሌር ጦር መሳሪያ እንደማትፈልግ በተደጋጋሚ ተናግራለች። ነገር ግን ማወቅ ያለብን የመተማመን ክፍተት እንዳለ ነው” ብለዋል።

    “ጦርነቱ እንዲቆም እና ወደ ድርድር እንዲመለሱ እማጸናለሁ” ብለዋል።

  4. ኢራን በእስራኤል ጥቃት የተፈጸመባት “ከአሜሪካ ጋር ተስፋ ሰጪ ውይይት ላይ ባለችበት ወቅት” መሆኑን አስታወቀች

    እስራኤል በኢራን እየፈጸመችው ያለውን ጥቃት የሚቃወም ሰልፍ በዩናይትድ ኪንግደም

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, እስራኤል በኢራን እየፈጸመችው ያለውን ጥቃት የሚቃወም ሰልፍ በዩናይትድ ኪንግደም

    ኢራን በእስራኤል ያልተጠበቀ ጥቃት የተፈጸመባት "ከአሜሪካ ጋር የኒውክሌር አቅምን አስመልክቶ ተስፋ ሰጪ ዲፕሎማሲያዊ ሂደት ላይ በነበረችበት ወቅት" መሆኑን አስታወቀች።

    ይህንን የተናገሩት የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሰብዓዊ መብቶች ምክር ቤት በጄኔቫ ግጭቱን አስመልክቶ በመከረበት ስብሰባ ላይ ነው።

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ እስራኤል በአገራቸው ላይ ያደረሰችው ጥቃት “ለሰው ልጅ ስልጣኔ ታሪካዊ ወቅት ነው” በማለት አገራት ለአለም አቀፍ ህግ መቆም እንዳለባቸው አሳስበዋል።

    አባስ አራግቺ እስራኤል በአገራቸው ላይ የፈጸመችውን ድንገተኛ ጥቃት "የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ቻርተርን የሚጥስ እንዲሁም ይህ ምክር ቤት የቆመበትን መርህ የሚጻረ"ር ሲሉ ገልጸውታል።

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ይህንን የተናገሩት በኢራን እና በእስራኤል መካከል ያለውን ግጭት ለማርገብ እንዲሁም በኢራን የኒውክሌር አቅምን ወደ ዲፕሎማሲያዊ ድርድር ለመመለስ ከዩናይትድ ኪንግደም፣ ከፈረንሳይ እና ከጀርመን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ጋር ከመነጋገራቸው በፊት ነው።

    በጥቃቶቿ ያሰበችውን ዕቅድ እንዳላሳካች የምትገልጸው እስራኤል በጥቃቷ የመቀጠል እቅድ አላት።

    ኢራን ሰላማዊ የኒውክሌር ኃይልን የማበልጸግ መብት እንዳላት ትናገራለች። እስራኤል ይህንን አትቀበለውም።

  5. የፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት ኢራን ለመደራደር ፈቃደኝነቷን ልታሳይ ይገባል አሉ

    የፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት ኢማኑኤል ማክሮን

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት ኢማኑኤል ማክሮን ከእስራኤል ጋር ያለውን ግጭት ለማስቆም ፈረንሳይን ጨምሮ አውሮፓውያኑ አገራት ለኢራን የዲፕሎማሲ ፕሮፖዛል እንደሚያቀርቡ ተናግረዋል።

    ማክሮን ፕሮፖዛሉ በአራት ዋና ዋና ክፎሎች መዋቀሩን ገልጸዋል።

    • የዓለም አቀፉ የአቶሚክ ኤነርጂ ኤጀንሲ (IAEA) በኢራን ስራውን እንዲጀምር እና የዩራኒየምን ማበልጸግ ስራ ወደ ዜሮ ማሸጋገር
    • የኢራንን የባለስቲክ ሚሳኤል እንቅስቃሴ መቆጣጠር
    • ኢራን በቀጣናው ላሉ ተዋጊ ቡድኖች የምታደርገውን የገንዘብ ድጋፍ በተመለከተ
    • በኢራን ውስጥ ያሉ “ታጋቾችን” ነጻ ማውጣት ይህም በኢራን እስር ቤቶች ውስጥ የታሰሩ የውጭ ዜጎችን የሚመለከት ነው

    “ኢራን የምናስቀምጠው ፕሮፖዛልን በተመለከተ በመድረኩ ተገኝታ ለመደራድር ፈቃደኛ መሆን አለባት” ሲሉ ማክሮን ለጋዜጠኞች ተናግረዋል።

  6. ስምንተኛ ቀኑን በያዘው የእስራኤል እና ኢራን ግጭት የተፈጠሩ አዳዲስ ክስተቶች

    የኢራን ጥቃት ተቃውሞ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    እስራኤልና ኢራን በሰማይ ላይ የሚያደርጉት ግጭት ስምንተኛ ቀኑን ይዟል።

    • የእስራኤል ጦር፣ የኢራን የኒውክሌር ምርምር ኤጀንሲ ዋና መስሪያ ቤትን ጨምሮ ከ60 በላይ የሚሆኑ ይዞታዎችን በቴህራን እና በሌሎች ስፍራዎች ላይ ማጥቃቱን አስታውቋል።
    • የኢራን ሚሳኤል በደቡባዊ እስራኤል ቤርሼባ ከተማ የሚገኝ የቴክኖሎጂ ፓርክ መምታቱን ተከትሎ በርካታ ህንጻዎች ወድመዋል። ሞት ባይከሰትም ሰባት ሰዎች ግን በደረሰባቸው ጉዳት ወደ ሆስፒታል ተወስደዋል።
    • የዩናይትድ ኪንግደም፣ የአውሮፓ ህብረት፣ የጀርመን እና የፈረንሳይ ከፍተኛ ዲፕሎማቶች ከኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺን ጋር በጄኔቫ ይገናኛሉ። ስምንት ቀናት ባስቆጠረው ግጭት ኢራን ከምዕራባውያኑ ጋር ፊት ለፊት ስትወያይ የመጀመሪያዋ ነው።
    • የጄኔቫ ውይይቶች እንደታቀደው የሚቀጥል ከሆነ በዚህ ቀውስ ውስጥ ትልቁን የአውሮፓ ተሳትፎ እንደሚያመለክት የቢቢሲ አለም አቀፍ ዘጋቢ አስነብቧል።
    • የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ እስራኤል ጥቃቷን እስካላቆመች ድረስ ሃገራቸው ከአሜሪካ እንደማትደራደር መናገራቸውን የመንግሥት ሚዲያዎች ዘግበዋል።
  7. የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ ማን ናቸው?

    የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ዛሬ በጄኔቫ ከፍተኛ የአውሮፓ ዲፕሎማቶች እና የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ የእስራኤል እና የኢራንን ግጭት ለማርገብ ይረዳል በሚል ውይይት ያደርጋሉ።

    ለመሆኑ አራግቺ ማን ናቸው?

    አባስ አራግቺ ከአውሮፓውያኑ 1989 ጀምሮ በኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ውስጥ ከሰሩ በኋላ ካለፈው ዓመት ነሐሴ ወር ጀምሮ የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሆነው ተሹመዋል።

    በፊንላንድ እና በጃፓን አምባሳደር በመሆንም አገልግለዋል።

    በይበልጥ የሚታወቁት ግን ከተባበሩት መንግሥታት የፀጥታው ምክር ቤት እና ከጀርመን ጋር በተደረገ ድርድር የኢራን ዋና ተደራዳሪ በመሆን በመሳተፋቸው ነው።

    ይህ ውይይት በ2015 የኢራን የኒውክሌር ስምምነት እንዲፈረም አስችሏል።

    በስምምነቱ መሰረት ኢራን የኒውክሌር እንቅስቃሴዋን ለመገደብ እና ዓለም አቀፍ ተቆጣጣሪዎችን ለመፍቀድ የፈረመች ሲሆን በምትኩ የኢኮኖሚ ማዕቀብ እንዲነሳላት ተስማምታለች።

    ዶናልድ ትራምፕ በ2018 አሜሪካን ከዚህ ስምምነት አስወጥተዋል።

  8. የኢራን ቴሌቪዥን ግጭቱን እንዴት እየዘገበ ነው?

    የኢራኑ ጠቅላይ መሪ በቴሌቪዥን መልዕክት ሲያስተላልፉ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የኢራን የመንግሥት ቴሌቪዥን እና ሌሎች ከመንግሥት ጋር ግንኙነት ያላቸው መገናኛ ብዙኃን ኢራን በእስራኤል ላይ የምትፈፅመውን የሚሳኤል እና ድሮን ጥቃት “የተሳካ” እና “ውጤታማ” ሲሉ ማድነቃቸውን ቀጥለዋል።

    ሆኖም እስራኤል በየቀኑ የምትፈፅመው ጥቃት በኢራናውያን ላይ እያሳደረ ያለውን ተፅዕኖ እና የከፍተኛ ወታደራዊ አዛዦችን ሞት ችላ ብለውታል።

    በምትኩ የኢራን ባለሥልጣናት ሕዝባቸው “በአንድነት እና በጽናት” እንዲቆሙ መልዕክት እያስተላለፉ ነው።

    በሚዲያ ላይ ከሚደረገው ጥብቅ ቁጥጥር እና “ የጠላት ፕሮፖጋንዳ” እንዳይሰራጭ ከሚሰጠው ማስጠንቀቂያ ጎን ለጎንም የእስራኤል “ ሰላዮች” ናቸው ተብለው የተጠረጠሩ ግለሰቦች እስር እንደቀጠለ ነው።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ ኢራናውያን የኢንተርኔት አገልግሎት መቋረጥና የሳይበር ጥቃት አጋጥሟቸዋል። በሳይበር ጥቃቱ ባንኮች ዒላማ ሆነዋል። ባለሥልጣናት ለዚህ እስራኤልን ተጠያቂ አድርገዋል።

    በኢንተርኔት ላይ ያጋጠመውን እገዳ ለማለፍ የሚያገለግለው ቪፒኤን በስፋት ተደራሽ አይደለም።

    በመሆኑም በኢራን የዕለት ተዕለት ሕይወት በክፍያ ፣ በነዳጅ እና በጥሬ ገንዘብ እጥረት እንዲሁም በመረጃ ውስንነት እየተፈተነ ነው።

  9. እስራኤል ጥቃቷን እስክታቆም ድረስ ከአሜሪካ ጋር ለንግግር ቦታ የለም - የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ

    የፎቶው ባለመብት, EPA-EFE/Shutterstock

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ የእስራኤል ጥቃት እስካልቆመ ድረስ አገራቸው ከአሜሪካ ጋር ለድርድር እንደማትቀመጥ መናገራቸውን የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    አራግቺ "አሜሪካውያን ድርድር ይፈልጋሉ፤እና ብዙ ጊዜ መልዕክት ልከዋል፤ ነገር ግን [ጥቃቱ እስኪቆም] ድረስ ለውይይት ምንም ቦታ እንደሌለ በግልጽ ተናግረናል።" ማለታቸው በመገናኛ ብዙኃኑ ዘገባ ላይ ተጠቅሷል።

    "በዚህ ወንጀል አጋር ከሆነችው ከአሜሪካ ጋር ምንም ዓይነት ንግግር የለንም።" ብለዋል ሚኒስትሩ።

    እስራኤል ጥቃት መፈጸም ከጀመረች በኋላ ለመጀመርያ ጊዜ አራግቺ ከምዕራባውያን መንግሥታት ጋር በሚደረገው ውይይት ላይ ለመገኘት ዛሬ በጄኔቫ ይገኛሉ ተብሎ ይጠበቃል።

    በዚህ ውይይት ላይ የአውሮፓ እና የዩኬ የውጪ ጉዳይ ሚኒስትሮችም ይሳተፋሉ።

  10. “ከግጭቱ ለመውጣት ያለው ብቸኛ አማራጭ ዲፕሎማሲ ነው” የዩኬ ሚኒስትር

    የዩናይትድ ኪንግደም የባህል፣ ሚዲያ እና ስፖርት ሚኒስትር ሊሳ ናንዲይ

    የፎቶው ባለመብት, EPA-EFE

    የዩናይትድ ኪንግደም የባህል፣ ሚዲያ እና ስፖርት ሚኒስትር ሊሳ ናንዲይ የኢራን እና እስራኤልን ግጭት ለማስቆም ብቸኛው አማራጭ ዲፕሎማሲ ነው አሉ።

    ሚኒስትሯ ይህን ያሉት ፕሬዚደንት ትራምፕ አገራቸው በሁለቱ አገራት ግጭት የሚኖራት ተሳትፎ ላይ ለመወሰን የሁለት ሳምንት ቀነ ገደብ ባስቀመጡበት ወቅት ነው።

    አሜሪካ ኢራን ላይ ጥቃት ለመፈፀም እስራኤልን ከተቀላቀለች ዩኬ እርምጃዋን ልትከተል ትችላለች ወይ ተብለው በቢቢሲ ራደዮ 5 የተጠየቁት ሚኒስትሯ፣ " ወሳኙ ነገር ግጭቱ እንዳይባባስ ማድረግ እንደሆነ" አፅንኦት ሰጥተዋል።

    በመከላከያ እና በደኅንነት ዙሪያ ብቸኛዋ የቅርብ አጋራችን ከሆነችው አሜሪካ ጋር በቅርበት እየሰራን ቢሆንም ካለው ሁኔታ የሚያወጣን "ግጭቱ እንዳይባባስ ማድረግ እና ዲፕሎማሲ ነው" ብለዋል።

    ሚኒስትሯ ጨምረውም በኢራን ያለውን "ያልተረጋጋ መንግሥት" እና "በጋዛ ያለውን የሰብዓዊ እርዳታ ቀውስ" በመጥቀስ በሕይወት ዘመናቸው መካከለኛው ምሥራቅ እንዲህ ዓይነት አስከፊ ሁኔታ ውስጥ ገብቶ እንደማያውቅ ተናግረዋል።

    “ በጣም በርካታ ፈተናዎች እየገጠሙን ነው።የሰዎችን ደኅንነት ለመጠበቅ እና ሰዎችን ለመደገፍ የሚረዳው መንገድ አንድ ነው - እርሱም ዲፕሎማሲ ነው።” ብለዋል።

  11. የአሜሪካ ምክር ቤት አባሏ ትራምፕ ግጭቱን የያዙበት መንገድ "እጅጉን አሳስቦኛል" አሉ

    የአሜሪካ ኮንግረስ አባል የሆነችው ትውልደ ኢራናዊት እና ዲሞክራቷ ያሳሚን አንሳሪ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የአሜሪካ ኮንግረስ አባል የሆኑት ትውልደ ኢራናዊት እና ዲሞክራቷ ያሳሚን አንሳሪ፣ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የእስራኤል እና የኢራን ግጭትን ያስተናገዱበት መንገድ “እጅግ አሳስቦኛል” አሉ።

    ለቢቢሲ ኒውስዴይ ፕሮግራም "በየቀኑ ሀሳቡን የሚቀይር ፕሬዝዳንት ነው ያለን" ያሉ ሲሆን፣ አክለውም "የሚናገረውን ማንም አያምንም" ብለዋል።

    የኢራቅ ጦርነትን በመጥቀስ ዩናይትድ ስቴትስ በቀጠናው ጥሩ ወይም "የተሳካ" ታሪክ ስለሌላት ጣልቃ መግባት እንደሌለባት ተናግረዋል።

    አንሳሪ ኢራናውያን ሥልጣን ላይ ያለው አካል አለመሆናቸውን ማስታወሱ አስፈላጊ እንደሆነ ጠቅሰው፣ አብዛኛው ሕዝብ ከ1979 ጀምሮ “በዕገታ ውስጥ” የያዛቸውን እስላማዊ ሪፐብሊክ እንደሚቃወሙ ገልጸዋል።

    በመሆኑም “በአገራቸው በቦምብ መደብደብ አይገባቸውም” ብለዋል።

    ትራምፕ ግጭቱን ለመፍታት ዲፕሎማሲያዊ መንገድ ላይ ትኩረት እንዲያደርጉ እና የአሜሪካ ወታደሮች "አላስፈላጊ የሕይወት መጥፋት" ወደ ሚወስድ መንገድ ላይ እንዳያተኩሩ አሳስበዋል።

  12. የእስራኤል ጥቃት አራክ የኒውክሌር ጣቢያን እንዳወደመ ዓለም አቀፉ የኢነርጂ ተቋም አረጋገጠ

    የኒውክሌር ጣቢያን የሚያሳይ የሳተላይት ምስል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    እስራኤል አራክ ከተማ አቅራቢያ በሚገኘውና በግንባታ ላይ በነበረው የኢራን የኒውክሌር ጣቢያ ላይ የፈፀመችው ጥቃት "ቁልፍ ሕንጻዎችን" እንዳወደመ ዓለም አቀፉ የኒውክሌር ተቆጣጠሪ አረጋገጠ።

    የእስራኤል የጦር አውሮፕላኖች ሐሙስ ዕለት አራክ የኒውክሌር ጣቢያን ደብድበዋል። ሆኖም ጣቢያው የኒውክሌር ቁሶችን አለመያዙን ዓለምአቀፉ የአቶሚክ ኢነርጅ ኤጀንሲ ገልጿል።

    ከደቡብ ምዕራብ ቴህራን በ250 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ እንደሚገኘው አራክ ያሉ የኒውክሌር ጣቢያዎች የሚያገለግሉት ለሳይንሳዊ ምርምር ሲሆን የኒውክሌር መሣሪያን ለመስራት የሚጠቅም ፕሉቶኒየም የተባለ ንጥረ ነገርን ያመርታሉ።

    የአቶሚክ ኢነርጂ ተቋሙ ዋና ዳይሬክተር ራፋኤል ግሮሲ በሰጡት መግለጫ እንዳሉት እስራኤል በፈፀመችው ጥቃት እስካሁን የተከሰተ የተለየ የጨረር ልቀት ባይኖርም፤ የመከሰት አደጋዎች ግን አሉ።

    “በዚህ ፈታኝ እና ውስብስብ በሆነ ሁኔታ ውስጥ ስለ ኒውክሌር ማዕከላቱ ጊዜውን የጠበቀ እና መደበኛ የሆነ ቴክኒካዊ መረጃዎችን ማግኘትም ወሳኝ ነው” ብለዋል።

  13. ኢራን በደቡባዊ እስራኤል የፈጸመችው ጥቃት በምስል

    በኢራን ጥቃት የተጎዳ ሕንጻ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    ትናንት ምሽት እስራኤል እና ኢራን ሚሳዔል ሲተኳኮሱ አምሽተዋል።

    የደቡብ እስራኤል ከተማ ቤርሳቤህ ከትናንት በስቲያ ከደረሰው ጥቃት በኋላ በድጋሚ ተመታለች።

    በትንሹ 71 ሰዎች ቆስለዋል ሲል የእስራኤል ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር አስታውቋል።

    የእስራኤል የድንገተኛ አደጋ አገልግሎት እንዳስታወቀው አምስት ሰዎች ትናንት ሌሊት በተፈጸመው ጥቃት ቆስለው ወደ ሆስፒታል ተወስደዋል። በመኖሪያ ሕንፃዎች ላይ የደረሰውን ጉዳት የሚያሳዩ ፎቶዎች አሁን ደርሶናል።

    በኢራን ጥቃት የተጎዳ አካባቢ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    በኢራን ጥቃት የተጎዱ መኪኖች

    የፎቶው ባለመብት, EPA

  14. በኢራን እና በእስራኤል መካከል ጥቃቶች ቀጥለዋል

    ፕሬዚደንት ዶናልድ ትራምፕ በእስራኤል እና በኢራን መካከል ለሚካሄደው የሰላም ድርድር የሁለት ሳምንት ጊዜ ቢሰጡም በሁለቱ አገራት መካከል ግን ሚሳኤሎች መወንጨፋቸውን አላቋረጡም።

    የእስራኤል ጦር በኢራን አየር ክልል ላይ ወደ 60 የሚጠጉ የእስራኤል ጄቶች በዋና ከተማዋ ቴህራን ዙሪያ እና ከኢራን የኒውክሌር መርሃ ግብር ጋር በተያያዙ ቦታዎች ላይ ዒላማዎችን መደብደባቸውን አስታውቋል።

    የእስራኤል መከላከያ የኢራን የኒውክሌር ምርምር ኤጀንሲ ዋና መሥሪያ ቤት ተመትቷል ሲል አስታውቋል።

    በተጨማሪም በርካታ የኢራን ሚሳኤል ማምረቻ፣ ማሰወንጨፊያ ስፍራዎችን ማውደሟን ገልጻለች።

    በምላሹ ኢራን ትናንት ጥቃት በፈጸመችበት በደቡባዊ እስራኤል ከተማ ቤርሳቤህ ድብደባ አካሄዳለች።

    ዒላማው የቴክኖሎጂ ፓርክ ሲሆን ትናንት ጥቃት ከደረሰበት ሆስፒታል አቅራቢያ የሚገኝ ነው።

    ኢራን አሁንም የእስራኤልን የአየር መከላከያ አይረን ዶም በማለፍ ረገድ ምን ያህል ውጤታማ እንደሆነች ያሳያል።

    በሌሎች የአገሪቱ ክፍሎች ከበፊቱ በተሻለ ፀጥ ያለ ሌሊት ነበር።

    ትናንት ምሽት በኢየሩሳሌምም ሆነ በቴልአቪቭ ምንም የአደጋ ጊዜ ደወል አልተሰማም።

  15. ዓለም ትራምፕ ቀጥሎ የሚወስኑትን ውሳኔ በጉጉት እየተጠባበቀ ነው

    ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በእስራኤል እና በኢራን መካከል ያለው ግጭት ስምንተኛ ቀኑን ያስቆጠረ ሲሆን፣ ዓለም ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ቀጥሎ የሚያደርጉትን ለማየት በጉጉት እየጠበቀ ነው።

    • በሚቀጥሉት ሁለት ሳምንታት ውስጥ እስራኤል ከኢራን ጋር በምታደርገው ጦርነት ውስጥ ለመሳተፍ ወይም ላለመሳተፍ ውሳኔ እንደሚሰጡ ፕሬዚዳንቱ ተናግረዋል።
    • የዋይት ሐውስ የፕሬስ ሴክሬታሪያት (ካሮሊን ሌቪት) ባነበቡት መግለጫ ላይ ትራምፕ ከኢራን ጋር “ትልቅ የመደራደር እድል አለ” ብለዋል።
    • ትራምፕ ኢራንን የማጥቃት ዕቅዳቸውን ያጸደቁ ቢሆንም ከእስራኤል ጎን ለመሰለፍ ወይንም ላለመሰለፍ አልወሰኑም ሲሉ ምንጮች ለቢቢሲ የአሜሪካ አጋር ሲቢኤስ ተናግረዋል።
    • ትራምፕ በፎርዶ በሚገኘው የኢራን የምድር ውስጥ የዩራኒየም ማበልፀጊያ ተቋም ላይ ጥቃት የመፈጸም ብርቱ ሃሳብ እንዳላቸው ሲቢኤስ ዘግቧል። የምድር ውስጥ የኒውክለር ተቋሙን ለማጥፋት የሚያስችል ትልቅ ቦምብ እንዳላት የሚታሰበው አሜሪካ ብቻ ናት።
  16. በደቡባዊ እስራኤል ኢራን በፈፀመችው ጥቃት በማይክሮሶፍት ቢሮ አካባቢ እሳት ተነሳ

    በደቡባዊ እስራኤል ማእክሮሶፍት ቢሮ አቅራብያ የተነሳ እሳት

    የፎቶው ባለመብት, Israel Firefighters

    በደቡባዊ እስራኤል ቤርሳቤህ ኢራን በፈጸመችው ጥቃት ከማይክሮሶፍት ቢሮዎች አጠገብ የእሳት ቃጠሎ የሚታይ ሲሆን በመኖሪያ ሕንፃዎች ላይ ጉዳት መድረሱን የወጡ ምስሎች ያሳያሉ።

    የእሳት አደጋ ሠራተኞች እና የሕክምና ባለሙያዎች በቦታው ተገኘኝተው እሳቱን ለማጥፋት እና የተጎዱ ሰዎችን ለመርዳት እየሞከሩ ነው።

    አምስት ሰዎች ቆስለው ወደ ሆስፒታል መወሰዳቸውን የእስራኤል የድንገተኛ አደጋ አገልግሎት አስታውቋል።

    ኢራን በዚህ ጥቃት በድጋሚ የጋቭ ያም የላቀ የቴክኖሎጂ ፓርክን ዒላማ አድርጋለች።

    የኢራን ባለስልጣናት ትናንት ማለዳ ላይ በፈፀሙት ጥቃት የሶሮካ ሆስፒታል በተመታበት ወቅት በአቅራብያው የሚገኝ ወታደራዊ ተቋም ላይ ማነጣጠራቸውን ተናግረው ነበር።

  17. በኢራን እና በእስራኤል ግጭት ያሉ አዳዲስ መረጃዎች

    ሐሙስ ዕለት በኢራን የሚሳዔል ጥቃት የተመታው የእስራኤል ሆስፒታል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ሐሙስ ዕለት በኢራን የሚሳዔል ጥቃት የተመታው የእስራኤል ሆስፒታል
    • የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ "በሚቀጥሉት ሁለት ሳምንታት ውስጥ" በኢራን ላይ ወታደራዊ ጥቃት ለመሰንዘር ውሳኔ ላይ እንደሚደርሱ ተናግረዋል።
    • ትራምፕ የሁለት ሳምንት ጊዜ የሰጡት ከኢራን ጋር ባለው " ትልቅ የመደራደር ዕድል" ምክንያት ሲሆን ይህ እርምጃ ውጥረቱን ይቀንሰዋል ተብሎ ተስፋ ተጥሏል።
    • ትራምፕ በመካከለኛው ምሥራቅ ግጭት ላይ ለመወሰን ሁለት ሳምንት ጊዜ ሲሰጡ ዩኬ እና የአውሮፓ ኅብረት ከኢራን ጋር ሊነጋገሩ ነው
    • ኢራን በእስራኤል ሆስፒታል ላይ በፈጸመው ጥቃት ቢያንስ 71 ሰዎች ቆስለዋል። ጥቃቱን ተከትሎ የእስራኤል መከላከያ ሚኒስትር እንዳሉት ይህ ጥቃት የሚያሳየው የኢራን ጠቅላይ መሪ "ከእንግዲህ ወዲያ እንዲኖር እንደማይፈቀድለት ነው" ብለዋል።
    • ኢራን በኢንተርኔት ላይ እገዳ ጥላለች፤ ይህም በአገሪቱ ታሪክ እጅግ የከፋ ነው ተብሏል።
    • አሜሪካ እና ዩኬ በውጪ ጉዳይ ሚኒስትሮቻቸው በኩል ባደረጉት ስብሰባ ኢራን “የኒውክሌር መሣርያ እንዳይኖራት” ከስምምነት ላይ ደርሰዋል።
    • የእንግሊዝ ውጪ ጉዳይ ሚኒስትር ከፈረንሳይ፣ ጀርመን፣ አውሮፓ ኅብረት እና የኢራን ባለሥልጣናት ጋር ዛሬ ከሰኣት በጄኔቫ ሊገናኙ ቀጠሮ ይዘዋል።
  18. አሜሪካ ወደ ጦርነቱ የምትገባ ከሆነ አካባቢው “ሲኦል” ይሆናል - የኢራን ባለሥልጣን

    ባለፈው እሁድ የተፈጸመ ጥቃት

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ሳምንት በሆነው እስራኤል በኢራን ላይ በከፈተችው ጥቃት አሜሪካ ለመሳተፍ እጇን የምታስገባ ከሆነ “ሲኦል” ይከሰታል ሲሉ የኢራን ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሳዒድ ኻቲብዛዴህ ለቢቢሲ ተናገሩ።

    አሜሪካ በኢራን ላይ በሚካሄደው ጥቃት የምትሳተፍ ከሆነ ኢራን ሁሉንም አማራጮች በጠረጴዛዋ ላይ መሆናቸውን በማመልከት "ይህም አጠቃላይ ቀጣናውን አረንቋ እና ሲኦል ያደርገዋል” ሲሉ አስጠንቅቀዋል።

    ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ሳዒድ ኻቲብዛዴህ ለቢቢሲ እንደተናገሩት አሁንም ኢራን ዲፕሎማሲያዊ መፍትሔ ምርጫዋ መሆኑን በመጥቀስ፤ ነገር ግን ጥቃቱ በኢራን ላይ የሚቀጥል ከሆነ “ማንም ወደ ድርድር ሊሄድ አይችልም” ብለዋል።

    ይህ ጦርነት “የአሜሪካ ጦርነት አይደለም” ያሉት ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ፣ “ትራምፕ የሚሳተፉ ከሆነ ግን በማያገባቸው ጦርነት የተሳተፉ ፕሬዝዳንት ሆነው እንደሚታወሱ ተናግረዋል።

    "እኛ የምናስበው ይህ ጦርነት አሜሪካንን የሚመለከት ጦርነት አይደለም፤ ነገር ግን ወደ ጦርነቱ መግባት የሚፈልጉ ከሆነ፣ ትራምፕ ለዘላለሙ ወደ ማይመለከታቸው ጦርነት ተጎትተው የገቡ መሪ ተብለው ሲታሰቡ ይኖራሉ” ብለዋል።

    በዋናነት የኢራንን የሚሳዔል እና የኒውክሌር ተቋማትን ዒላማ አድርጋ ጥቃቶችን በመፈጸም የሰነበተችው እስራኤል ከመሬት በታች የሚገኙ ያለቻቸውን የኒውክሌር ተቋማትን ለማውደም የአሜሪካን ድጋፍ እየጠየቀች ነው።

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ እስካሁን ኢራንን ለማጥቃት ከእስራኤል ጋር እንደሚያብሩ የሚያመለክት ግልጽ ምላሽ ባይሰጡም፤ በኢራን ላይ የሚፈጸም ጥቃትን ማጽደቃቸውን በተመለከተ የአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን እየዘገቡ ነው።

  19. እስራኤል እና ኢራን እየተወዛገቡበት ያለው የሆስፒታል ጥቃት

    ዛሬ በኢራን ሚሳዔል መመታቱ የተነገረው ቤርሻባህ ውስጥ የሚገኘው ሶሮካ ሆስፒታል ላይ በተፈጸመው ጥቃት 71 ሰዎች መቁሰላቸውን የእስራኤል ጤና ባለሥልጣናት አስታውቀዋል።

    ኢራን ግን ዒላማ ያደረገችው ከሆስፒታሉ አቅራቢያ የሚገኝ ወታደራዊ ተቋምን ነው በማለት የቀረበባትን ክስ አስተባብላለች።

    የእስራኤል ባለሥልጣናት ግን በሆስፒታሉ ላይ የተፈጸመው ጥቃት “ሆን ተብሎ” ዒላማ መደረጉን በመጥቀስ “ወንጀል ነው” ሲሉ ከሰዋል።

    በተባበሩት መንግሥታት የኢራን ተልዕኮ በኤክስ ላይ ጥቃቱን አስመልክቶ በሰጠው ምላሽ የእስራኤልን ክስ “ሐሰተኛ” በማለት ውድቅ ከማድረጉ በተጨማሪ፣ ጥቃቱ እስራኤል በኢራን ላይ የምትፈጽመውን ጥቃት “በመደገፍ የሚሳተፍ ተቋም ላይ” መሆኑን እና “በትክክል” ዒላማውን የመታ ነው ብሏል።

    ቀደም ሲል የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ ጥቃቱ የእስራኤልን ወታደራዊ የዕዝ ማዕከል ዒላማ ያደረገ መሆኑን ገልጸው “የፍንዳታው ንዝረት” በሆስፒታሉ ላይ “ቀላል ጉዳት አድርሷል” ብለዋል።

    ሐሙስ አመሻሽ ላይ በሆስፒታሉ ላይ የደረሰውን ጉዳት የሚያሳዩ ምሥሎች በተለያዩ የዜና ወኪሎች እየወጡ ሲሆን፣ የተወሰኑትን እነሆ. . .

    ሆስፒታሉ ጥቃት ከደረሰበት በኋላ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ሆስፒታሉ ጥቃት ከደረሰበት በኋላ
    በሆስፒታሉ ላይ የደረሰ ጉዳት ከውጪ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, በሆስፒታሉ ላይ የደረሰ ጉዳት ከውጪ
    በሆስፒታሉ ላይ የደረሰ ጉዳት ከውስጥ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, በሆስፒታሉ ላይ የደረሰ ጉዳት ከውስጥ
    ጠቅላይ ሚኒስትር ኔታኒያሁ ሆስፒታሉን በጎበኙበት ጊዜ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ጠቅላይ ሚኒስትር ኔታኒያሁ ሆስፒታሉን በጎበኙበት ጊዜ
  20. ኢራን በእስራኤል ላይ ዛሬ በፈጸመቻቸው ጥቃቶች 71 ሰዎች መጎዳታቸው ተነገረ

    በኢራን ሚሳዔል ዛሬ ከተመቱ ሕንጻዎች አንዱ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የምስሉ መግለጫ, በኢራን ሚሳዔል ዛሬ ከተመቱ ሕንጻዎች አንዱ

    ኢራን ዛሬ በእስራኤል ላይ በፈጸመቻቸው ጥቃቶች 271 ሰዎች መቁሰላቸውን የአገሪቱ ጤና ሚኒስቴር ያሳወቀ ሲሆን፣ ከእነዚህ ውስጥ 71ዱ የተጎዱት ሶሮካ ሆስፒታል ላይ በተፈጸመ ጥቃት መሆኑ ተነግሯል።

    "ቀላል ጉዳት ከደረሰባቸው አብዛኞቹ የቆሰሉት ጥበቃ ወደ'ሚደረግላቸው ቦታዎች ሲወሰዱ ወይም በድንጋጤ ምክንያት” መሆኑን የእስራኤል ጤና ሚኒስቴር በኤክስ ገጹ ላይ አስታውቋል።

    ግጭቱ ከተጀመረበት ካለፈው ሳምንት አንስቶ እስከ ትናንት ድረስ ኢራን በፈጸመቻቸው የሚሳዔል ጥቃቶች ቢያንስ 24 ሰዎች ሲገደሉ፣ 592 ሰዎች ደግሞ ቆስለዋል።

    የኢራን ባለሥልጣናት በእስራኤል ጥቃት ስለደረሰው ጉዳት በዛሬው ዕለት እስካሁን መረጃ አላወጡም።

    ካለፈው አርብ ጀምሮ እስከ ትናንት ረቡዕ ድረስ በእስራኤል ጥቃት 224 ኢራናውያን ሲገደሉ ከ1 ሺህ 200 በላይ የሚሆኑ ሰዎች ደግሞ ቆስለዋል።

    መቀመጫውን ዋሽንግተን ያደረገው እና ለረጅም ጊዜ ኢራንን ሲከታተል የቆየው ሂዩማን ራይትስ አክቲቪስትስ ኒውስ ኤጀንሲ የተባለው ድርጅት ግን ኢራን ውስጥ የተገደሉትን ሰዎች ቁጥር ወደ 639 ያደርሰዋል።