ትራምፕ ከኢራን ጋር “ጠንከራ ንግግር” ተጀምራል ሲሉ ቴህራን ወታደራዊ ልምምድ ለማድረግ እየተዘጋጀች ነው

የአሜሪካ ጦር በባሕር ሰላጤው አካባቢው ያለውን ይዞታ ማጠናከሩን ተከትሎ ኢራን ከዩኤስ ጋር ምክክር መጀመሯን ፕሬዝደንቱ ጠቁመዋል። በሌላ በኩል ኢራን ለዓለም ንግድ ወሳኝ በሚባለው እና የመርከቦች መተላለፊያ በሆነው ሆርሙዝ ሰርጥ ለሁለት ቀናት የሚቆይ ወታደራዊ ልምምድ እንደምታደርግ ይጠበቃል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ትራምፕ፡ ኢራን ከአሜሪካ ጋር “ጠንከር ያለ ንግግር” ጀምራለች

    ፕሬዝደንት ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የአሜሪካው ፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ ኢራን ከአሜሪካ ጋር “ጠንከር ያለ ንግግር ጀምራለች” አሉ።

    የአሜሪካ ጦር በባሕር ሰላጤው አካባቢው ያለውን ይዞታ ማጠናከሩን ተከትሎ ኢራን ከዩኤስ ጋር ምክክር መጀመሯን ፕሬዝደንቱ ጠቁመዋል።

    በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለው ውጥረት እየተካረረ የመጣ ሲሆን ትራምፕ ውይይት “ተቀባይነት” ያለው ውጤት እንደሚያመጣ ተስፋ እንዳላቸው ተናግረዋል።

    የኢራን ከፍተኛ የደኅንነት ባለሥልጣን የሆኑት አሊ ላሪጃኒ ድርድር ለማድረግ የሚደረገው ማዕቀፍ ሒደት ማሳየቱን ተናግረዋል።

    ኢራን ኒውክሌር ለማብላላት የምታደርገውን ጥረት ተከትሎ ጣልቃ እንደሚገቡ ሲዝቱ የቆዩት ትራምፕ በቅርቡ የተካሄደውን ሕዝባዊ አመፅ አስታከው ጥቃት እንደሚሰነዝሩ ተናግረዋል።

    ቴህራን በበኩሏ በየብስም ሆነ በምድር ለሚሰነዘር ጥቃት “አፀፋዊ እና ከባድ ምላሽ” እንደምትሰጥ አስጠንቅቃለች።

    ኢራን ለዓለም ንግድ ወሳኝ በሚባለው እና የመርከቦች መተላለፊያ በሆነው ሆርሙዝ ሰርጥ ለሁለት ቀናት የሚቆይ ወታደራዊ ልምምድ እንደምታደርግ ይጠበቃል።

    ኢራን የአሜሪካ ኃይሎች ባሉበት አካባቢ የትኛውንም ዓይነት “ደኅንነቱ ያልተጠበቀ እና ፕሮፌሽናል ያልሆነ ባሕሪ” እንዳታሳይ ዩኤስ አስጠንቅቃለች።

    አሜሪካ ዩኤስኤስ አብርሀም ሊንከን የተሰኘው ግዙፍ የጦር መርከብን ጨምሮ በርካታ የጦር ኃይሎቿን ወደ ባሕረ ሰላጤው አሰማርታለች።

    ቅዳሜ ዕለት ሁለት ፍንዳታዎች መሰማታቸው በሀገሪቱ ውጥረት እንዲነዛ አድርጓል። የኢራን መንግሥት ፍንዳታዎቹ የተከሰቱት በጋዝ ምክንያት ነው ብሏል።

  2. ኢራን የአውሮፓ ሀገራት የጦር ሠራዊቶችን “አሸባሪ” ስትል ፈረጀች

    የኢራን ፓርላማ ቃል አቀባይ ሞሐመድ ባቄር ቃሊባፍ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ኢራን የአውሮፓ ሀገራትን የጦር ሠራዊቶች “አሸባሪ ቡድኖች” ስትል መፈረጇን የኢራን ፓርላማ አፈ-ጉባዔ ሞሐመድ ባቄር ቃሊባፍ ተናገሩ።

    አፈ-ጉባዔው እሑድ የኢራን አብዮታዊ ዘብን አሸባሪ ቡድን ነው ያሉ የአውሮፓ ሀገራት መከላከያ ሠራዊቶችን በሽብር ቡድን መፈረጃቸውን ሮይተርስ የዜና ወኪል ዘግቧል።

    የአውሮፓ ኅብረት ባለፈው ሐሙስ የኢራን አብዮታዊ ዘብን ሽብርተኛ ቡድን ብሎ መፈረጁ ይታወሳል።

    ባለፈው ታኅሣሥ በኢራን የተቀሰቀሰው ተቃውሞ በአውሮፓውያኑ 1979 ከተካሄደው እስላማዊ አብዮት በኋላ ደም አፋሳሹ ነበር ተብሏል።

    “አውሮፓውያኑ አብዮታዊ ዘቡን እንመታለን ብለው እግራቸውን ነው በጥይት የመቱት። ከሕዝባቸው በተቃራኒ ቆመው በጭፍን የአሜሪካን ፍላጎት እያሟሉ ነው” ሲሉአፈ-ጉባዔው ለሕዝብ እንደራሴዎች ተናግረዋል።

    የፓርላማው አባላት የአብዮታዊ ዘቡን ዩኒፎርም አድርገው በመገኘት ለልዩ ኃይሉ ያላቸውን ድጋፍ ገልፀዋል።

    “አብዮታዊ ዘቡን ሽብርተኛ ቡድን ብሎ የፈረጀ ሽብርተኛ ድርጅት ተደርጎ ይቆጠራል የሚለውን አንቀፅ 37” በማጠቀስ ቃል-አቀባዩ የአውሮፓ ሀገራት ጦር ሠራዊቶችን ሽብርተኛ ሲሉ ፈርጀዋል።

    ቃሊባፍ አክለው በቴህራን የሚገኙ የአውሮፓ ሀገራት ወታደራዊ አታሼዎች ከሀገር በሚባረሩበት ጉዳይ የፓርላማው የብሔራዊ ደኅንነት ኮሚሽን እንደሚመክር አስታውቀዋል።

    ከ1979 የኢራን አብዮት በኋላ የሺያት አገዛዝ ቡድን አባላትን ለመከላከል የተቋቋመው አብዮታዊ ዘብ በሀገሪቱ ትልቅ ቦታ የሚሰጠው ሲሆን ምጣኔ ሀብቱንና ጦር ሠራዊቱን እንደሚቆጣጠር ይታመናል።

  3. በዲሞክራቲክ ኮንጎ የማዕድን ማውጫ ሥፍራ ተደርምሶ ከ200 በላይ ሰዎች ሞቱ

    የማዕድን ሥፍራ

    የፎቶው ባለመብት, Hassan Lali / BBC

    የምስሉ መግለጫ, አሁን ላይ በአማጺያኑ ቁጥጥር ሥር የሚገኘው የማዕድን ማውጫ በጥሩ ሁኔታ የተያዘ እንዳልሆነ ምንጮች ተናግረዋል

    በዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ምሥራቃዊ ክፍል የማዕድን ማውጫ ተደርምሶ ከ200 በላይ ሰዎች መሞታቸውን በአካባቢው የሚንቀሳቀሰው አማጺ ቡድን ባለሥልጣናት ተናገሩ።

    የአማጺ ቡድኑ የሰሜን ኪቩ ግዛት አስተዳዳሪ ቃል አቀባይ ሉሙምባ ካምቤሬ ሙይሳ፣ የማዕድን ማውጫ ሥፍራው በከባድ ዝናብ ምክንያት ባለፈው ረቡዕ መደርመሱን ለጋዜጠኞች ተናግረዋል። ሆኖም በጊዜው የሟቾችን ቁጥር በትክክል ማወቅ አልተቻለም ነበር።

    ዘመናዊ ስልኮችን እና ኮምፒዩተሮችን ጨምሮ የኤሌክትሮኒክስ ቁሳቁሶችን ለመስራት የሚውለውን ኮባልት ማዕድን በማውጣት ላይ ሳሉ ከሞቱት ማዕድን አውጭዎች መካከል ሴቶች እና ሕፃናት ይገኙበታል።

    ወደ 20 የሚሆኑ ሰዎች ከአደጋው የተረፉ ሲሆን ሕክምና እየተደረገላቸው ይገኛል።

    እነዚህ የአደጋው ሰለባዎች በማዕድን አውጭ ተቋም የተቀጠሩ አይደሉም።

    አካባቢው በጥሩ ሁኔታ የተያዘ ባለመሆኑ በተደጋጋሚ አደጋዎች እንዲደርሱ እና አደጋ ከደረሰ በኋላም የነፍስ አድን ሥራን አዳጋች እንዳደረገው የቀድሞው የአካባቢው ተቆጣጣሪ ለቢቢሲ ተናግረዋል።

    አማጺው ቡድን ኤም23 ሰሜናዊ ኪቩ ግዛትን ከተቆጣጠረ በኋላ የተሾሙት የአካባቢው አስተዳዳሪ ኢራስቶ ባሃቲ ሙሳንጋ አርብ ዕለት ከአደጋው የተረፉ ሰዎችን ጎብኝተዋል።

    አደጋው የደረሰባት ሩባያ በጎረቤት አገር ሩዋንዳ ይደገፋል በሚባለው ኤም23 አማጺ ቡድን ቁጥጥር ሥር ከሚገኙ የሰሜን ኪቩ ከተማዎች አንዷ ናት።

    በዓለም ካለው የኮባልት ማዕድን አቅርቦት 15 በመቶ የሚሆነው እና በአገሪቷ ካለው ግማሽ የሚሆነው የሚገኘውም በዚችው ሩባያ ከተማ ነው።

  4. የኢራኑ ፕሬዝደንት: አሜሪካ፣ እስራኤል እና አውሮፓውያን “ሰዎች ሀገራችንን እንዲበትኑ ቀስቅሰዋል”

    የኢራኑ ፕሬዝደንት ማሱድ ፔዜሽኪያን

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የኢራኑ ፕሬዝደንት ማሱድ ፔዜሽኪያን ዩናይትድ ስቴትስ፣ እስራኤል እና የአውሮፓ መሪዎች የኢራንን ምጣኔ ሀብታዊ ቀውስ በመጠቀም አለመረጋጋት እንዲፈጠር እና ሰዎች “ሀገራችንን እንዲበትኑ” ምክንያት ለመሆን ሞክረዋል ሲሉ ወቀሱ።

    ሮይተርስ የዜና ወኪል እንደዘገበው ፕሬዝደንቱ ቅዳሜ በብሔራዊ የቴሌቪዥን ጣቢያ በተላለፈ ንግግራቸው አሜሪካ፣ እስራኤል እና አውሮፓውያን “ክፍፍል እንዲፈጠር እና ተቃውሞው እንዲነሳ ቀስቅሰው አንዳንድ ንፁሕ ሰዎች ወደዚህ እንቅስቃሴ እንዲገቡ አድርገዋል” ሲሉ ከስሰዋል።

    በኢራን ባለፈው ታኅሣሥ በምጣኔ ሀብት ቀውስ ምክንያት ተነስቶ ለሁለት ሳምንታት በቆየው ተቃውሞ 6 ሺህ 563 ሰዎች መገደላቸውን መቀመጫውን አሜሪካ ያደረገው ኤችአርኤኤንኤ የተባለው ድርጅት አስታውቋል።

    ድርጅቱ ከሟቾቹ መካከል 6 ሺህ 170 የሚሆኑት ተቃዋሚዎች ናቸው ብሏል። 214 የሚሆኑት ደግሞ የፀጥታ አካላት መሆናቸውን ገልጿል።

    የኢራኑ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ 3 ሺህ 100 ሰዎች መገደላቸውን እና ከእነዚህ መካከል 2 ሺህ የሚሆኑት የፀጥታ ኃይሎች መሆናቸውን ለሲኤንኤን ተርክ ተናግረዋል።

    የአሜሪካው ፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ በተደጋጋሚ ለተቃዋሚዎቹ ያላቸውን ድጋፍ የገለፁ ሲሆን ኢራን ሰልፈኞቹን መግደል የማታቆም ከሆነ እርምጅ እንደሚወስዱ ዝተው ነበር።

    የአሜሪካ ባለሥልጣናት አርብ ዕለት ትራምፕ የሚወስዱት እርምጃ ላይ እየመከሩ እንደሆነ ተናግረዋል።

    ኢራን ሚሳዔሎቿን እና መከላከያ ሥርዓቷን በተመለከተ “መቼም ቢሆን” እንደማትደራደር ብታሳውቅም ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ግን “ለስምምነት ዝግጁ መሆናቸውን ልነግራችሁ እችላለሁ” ብለዋል። ኢራን ወታደራዊ እርምጃ ከሚወሰድባት ይልቅ ከአሜሪካ ጋር መስማማትን እንደምትመርጥም ትራምፕ ተናግረዋል።

  5. አሜሪካ ለእስራኤል እና ሳዑዲ አረቢያ በ16 ቢሊየን ዶላር ጦር መሣሪያዎችን ልትሸጥ ነው

    አፓቼ የውጊያ ሄሊኮፕተር
    የምስሉ መግለጫ, እስራኤል 30 አፓቼ የውጊያ ሄሊኮፕተር ትገዛለች

    የፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አስተዳደር ወደ 16 ቢሊየን ቢሊየን የሚጠጋ ዶላር የሚከፈልባቸው የተለያዩ ዘመናዊ የጦር መሣሪያዎችን ለእስአኤል እና ለሳዑዲ አረቢያ እንዲሸጡ ፈቀደ።

    ይህ በአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት በኩል ይፋ የተደረገው የባለብዙ ቢሊየን ዶላር የአሜሪካ የጦር መሣሪያ ሽያጭ የተፈቀደው በባሕረ ሰላጤው አካባቢ አሜሪካ በኢራን ላይ ጥቃት ትፈጽማለች በሚል ከፍተኛ ውጥረት በተፈጠረበት ጊዜ ነው።

    የጦር መሣሪያዎቹ የሚሸጡት ደግሞ የኢራን ዋነኛ ጠላት ለሆነችው እስአኤል እና በዐይነ ቁራኛ ለምትጠብቃት ሳዑዲ አረቢያ ነው።

    አሜሪካ በዚህ ውሳኔዋ ከፍተኛ ገንዘብ የሚያስገኘው የጦር መሣሪያን በዘጠኝ ቢሊየን ዶላር ለሳዑዲ አረቢያ እንዲሁም ከ6.5 ቢሊየን ዶላር በላይ ደግሞ ለእስራኤል ሽያጭ ይፈጸማል።

    የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባወጣው መረጃ በ4 ቢሊየን ዶላር በሚጠጋ ገንዘብ 30 አፓቼ የተባሉ የጦር ሄሊኮፕተሮች እና በቀሪ ውደግሞ የእግረኛ ወታደሮች የውጊያ ተሽከርካሪዎች ለእስራኤል ይሸጥላታል።

    በተጨማሪም የአሜሪካ የመከላከያ መሥሪያ ቤት ፔንታጎን እንዳስታወቀው ሳዑዲ አረቢያ ከ700 በላይ ፓትሪየት ሚሳዔሎች እና ተያያዥ የጦር መሳሪያዎች እንድትገዛ ተፈቅዶላታል።

  6. በአሜሪካ በርካታ ከተሞች ውስጥ የኢሚግሬሽን ፖሊስን የሚቃወሙ ሰልፎች ተካሄዱ

    ሰልፍ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የአሜሪካ የፌደራል ኃይሎች ሁለት ዜጎችን መግደላቸውን ተከትሎ በሚኒያፖሊስ ከተማ የተነሳውን ተቃውሞ የተቀላቀሉ በሺህዎች የሚቆጠሩ ሰልፈኞች በአሜሪካ በርካታ ከተማዎች ተቃውሟቸውን አሰሙ።

    ኒውዮርክ፣ሎስ አንጀለስ፣ ቺካጎ እና ዋሽንግተን ዲሲን ጨምሮ በተለያዩ የአሜሪካ ከተሞች ተቃውሞዎች ተካሂደዋል። የሰልፉ አዘጋጆቹ አሜሪካውያን ከሥራ እና ከትምህርት ቤት በመቅረት ተቃውሟቸውን እንዲያሰሙ ጥሪ አቅርበዋል።

    "ብሔራዊ መዘጋት" ተብሎ የተጠራው የዚህ ተቃውሞ ሰልፍ አዘጋጆች፤ ስራ፣ ትምህርት እና ግብይት እንዲቆም እንዲሁም የፌደራል ኢሚግሬሽን እና ጉምሩክ ፖሊሶች የሚደረገው የገንዘብ ድጋፍ እንዲቆም እየጠየቁ ነው።

    በአዘጋጆቹ ድረ ገጽ ላይ የወጣው መረጃ እንደሚያመለክተው፤ ሰልፉ ተዘጋጀው ሬኔ ጉድ እና አሌክስ ፕሬቲን ጨምሮ በፌደራል ኃይሎች የተገደሉ ሰዎች ምክንያት በማድረግ ነው።

    የፌደራል ኢሚግሬሽን እና ጉምሩክ ፖሊሶች ሬኔ ጉድ እና አሌክስ ፕሬቲ የተባሉ አሜሪካውያን መግደላቸው ሚኒሶታ ግዛት ውስጥ ተቃውሞ ያስነሳ ሲሆን በመላ አገሪቱም ቁጣን አስከትሏል። ዴሞክራት እና ሪፐብሊካን ሆኑ ሕግ አውጪዎችም የፌደራል ኃይሎቹን እርምጃ ተችተዋል።

    የአሜሪካ የፍትሕ መስሪያ ቤት የጽኑ ሕክምና ነርስ የሆነው ፕሬቲን ሞት በተመለከተ የሲቪል መብቶች ምርመራ ከፍቷል። የ37 ዓመቱ ነርስ ሚኒያፖሊስ የተሰማሩት የፌደራል ኃይሎች ተኩሰው የገደሉት ሁለተኛው ሰው ሆኗል።

    ሐሙስዕለት የድንበር ጉዳዮች ኃላፊው ቶም ሆማን የሚኒሶታ ባለስልጣናት የሚተባበሩ ከሆነ ግዛቱ ውስጥ የተሰማራው የፌዴራል ኃይል ቁጥር “እንዲቀነስ” ሊደረግ እንደሚችል ጠቁመዋል።

  7. ደቡብ አፍሪካ እና እስራኤል አንዳቸው የሌላኛቸውን ዲፕሎማት አባረሩ

    ደቡብ አፍሪካ እስራኤልን በፍልስጤም ጉዳይ በዓለም አቀፍ ፍርድ ቤት ከከሰሰች በኋላ በአገራቱ መካከል ያለው ግንኙነት ሻክሯል።

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ደቡብ አፍሪካ እስራኤልን በፍልስጤም ጉዳይ በዓለም አቀፍ ፍርድ ቤት ከከሰሰች በኋላ በአገራቱ መካከል ያለው ግንኙነት ሻክሯል

    ደቡብ አፍሪካ “ዲፕሎማቲክ መርሕ ጥሰዋል” ያለቻቸውን ከፍተኛ የእስራኤል ዲፕሎማት ስታባርር፤ እስራኤልም የደቡብ አፍሪካ ልዑክን አባረረች።

    በደቡብ አፍሪካ የእስራኤል ዲፕሎማት ኤሪል ሲዳማ በ72 ሰዓታት ውስጥ ከደቡብ አፍሪካ እንዲወጡ ትዕዛዝ ባስተላለፈች በሰዓታት ልዩነት፤ እስራኤል የሚገኙት የደቡብ አፍሪካ የፍልስጤም ዲፕሎማት ሻውን ኤድዋርድ ባይኔቪልድት በ72 ሰዓታት ውስጥ እንዲወጡ እስራኤል አዝዛለች።

    ደቡብ አፍሪካ እስራኤልን በፍልስጤም ጉዳይ በዓለም አቀፍ ፍርድ ቤት ከከሰሰች በኋላ በአገራቱ መካከል ያለው ግንኙነት ሻክሯል።

    በደቡብ አፍሪካ የእስራኤል ዲፕሎማት በይፋ የማኅበራዊ ሚዲያ ገጽ ፕሬዝዳንት ሲሪል ራማፎሳን ከመተንኮሳቸው በተጨማሪ ያለ ፈቃድ የእስራኤል አመራሮችን ወደ ደቡብ አፍሪካ መጋበዛቸው ተገልጿል።

    የደቡብ አፍሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር “ዲፕሎማቱ መብታቸውን በዝብዘዋል” ሲል ከስሷል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትራቸው ጊድዮን ሳር “የደቡብ አፍሪካን ሐሰተኛ ውንጀላ እና መሠረተ ቢስ እርምጃን ተከትሎ” የአገሪቱን ዲፕሎማት ማባረራቸውን ገልጸዋል።

    እስራኤልም ሆነ ደቡብ አፍሪካ ያባረሯቸው ዲፕሎማቶች በየአገራቸው ከፍተኛ እርከን ላይ የነበሩ ናቸው። እስራኤል በደቡብ አፍሪካ፤ እንዲሁም ደቡብ አፍሪካም በእስራኤል አምባሳደር የላቸውም።

  8. ኢራን ወታደራዊ እርምጃ ከሚወሰድባት ከአሜሪካ ጋር መስማማት እንደምትመርጥ ትራምፕ ተናገሩ

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ኢራን ከአሜሪካ ጋር ስምምነት ላይ ለመድረስ “ዝግጁ ናት” አሉ።

    ኢራን ሚሳዔሎቿን እና መከላከያ ሥርዓቷን በተመለከተ “መቼም ቢሆን” እንደማትደራደር ብታሳውቅም ትራምፕ ግን “ለስምምነት ዝግጁ መሆናቸውን ልነግራችሁ እችላለሁ” ብለዋል።

    ኢራን ወታደራዊ እርምጃ ከሚወሰድባት ይልቅ ከአሜሪካ ጋር መስማማትን እንደምትመርጥ ትራምፕ ተናግረዋል።

    ባለፈው ሳምንት ረቡዕ የኢራንን የኒውክሌር ፕሮግራም በተመለከተ ድርድር ለማድረግ “ጊዜው እየተጠናቀቀ ነው” በማለት ሲዝቱ ነበር።

    የአሜሪካ ግዙፍ የጦር መርከቦች ወደ ኢራን መቃረባቸውን ተከትሎ ጦርነት ሊነሳ ይችላል በሚል ተሰግቷል።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አሁን ላይ ከአሜሪካ ጋር ሊደረግ የታቀደ ውይይት ባይኖርም፤ አገራቸው “የጋራ መከባበር እና መተማመን” ባለበት ሁኔታ ልትደራደር እንደምትችል ገልጸዋል።

    ኢራን የኒውክሌር ፕሮግራሟ ሰላማዊ ዓላማ ያነገበ እንደሆነ ትገልጻለች። አሜሪካ እና አጋሮቿ የኒውክሌር የጦር መሣሪያ እያበለጸገች ነው በሚል መክሰሳቸውንም ታጣጥላለች።

    ትናንት ክሬምሊን ይፋ ያደረገው መረጃ የኢራን የብሔራዊ ደኅንነት ኃላፊ አሊ ላሪጃኒ ከሩሲያው ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን ጋር መገናኘታቸውን ይጠቁማል።

    “የመካከለኛው ምሥራቅ እና ዓለም አቀፍ ጉዳዮችን” ጨምሮ በሌሎችም ርዕሰ ጉዳዮች ላይ መወያየታቸው ተገልጿል።

  9. “ኢራን ለድርድርም ሆነ ለጦርነት ዝግጁ ናት” የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አራግቺ

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ አገራቸው ለድርድርም ሆነ ለጦርነት ዝግጁ መሆኗን ቱርክ ውስጥ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ተናገሩ።

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ኢራን ወደ ድርድር እንድትመጣ ካልሆነ እርምጃ እንደሚወሰድባት እያስጠነቀቁ ባለበት ጊዜ ከቱርክ ባለሥልጣናት ጋር ለመነጋገር ያቀኑት የኢራኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አገራቸው ለሁለቱም ክስተቶች ዝግጁ መሆኗን ገልጸዋል።

    “የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ ድርድር ለማድረግ ምንም ችግር የለባትም፤ ነገር ግን ድርድር በማስፈራሪያ ጥላ ስር ሆኖ ሊደረግ አይችልም” ብለዋል።

    ባለሥልጣኑ ጨምረውም ኢራን ፍትሐዊ እና ትክክለኛ ድርድር ለማድረግ ዝግጁ መሆኗን እና በዚህ ጉዳይ ላይ ከቱርክ ጋር ግንኙነት እየተደረገ መሆኑን አመልክተዋል። ነገር ግን እስካሁን ከአሜሪካ ባለሥልጣናት ጋር ለመነጋገር “የተቆረጠ ጊዜ የለም።”

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አጽንኦት ሰጥተው አገራቸው እስላማዊ ሪፐብሊክ ኢራን “ለድርድር እና ለጦርነት” ዝግጁ መሆኗን ተናግረዋል።

    ኢራን ባለፈው ዓመት ሰኔ ከተካሄደው የ12 ቀናት ጦርነት በበለጠ ዝግጁ መሆኗን “አሁን አሜሪካ በቀጥታ ስለምትሳተፍ ሁኔታዎች ከቀደመው ጊዜ የተለየ ይሆናሉ። ምናልባትም ጦርነቱ ከሁለት አገራት ጦርነት በላይ ሊሆን ይችላል” ብለዋል።

    ከቱርኩ አቻቸው ጋር ጋዜጣዊ መግለጫውን የሰጡት የኢራኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አራግቺ አገራቸው "ትርጉም ባለው፣ ምክንያታዊ እና ፍትሐዊ” በመሆነ የዲፕሎማሲ ሂደት ውስጥ መሳተፍ እንደምትፈልግ ገልጸዋል።

    “በየትኛውም ሁኔታ በሌላ ወገን የሚመራ ወይም የሚጫን ውሳኔን ለመቀበል ፈቃደኛ አይደለንም” በማለት ከዚህ ቀደም በነበሩ ተሞክሮዎች “አሜሪካ በድርድር ወቅት በጎ ፈቃድ እና ታማኝነት ያንሳታል” በማለት ተችተዋል።

    ነገር ግን ኢራን ተገቢ እና ሕጋዊ ጥቅሟን በሚያስከብር እንዲሁም ስጋቷን በሚቀበል ሂደት ውስጥ ለመሳተፍ ፈቃደኛ መሆኗን ተናግረዋል።

    የኢራኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አሜሪካ ወታደራዊ ኃይሏን በኢራን አቅራቢያ እያሰባሰበች ባለችበት በአሁኑ ጊዜ በቱርክ አሸማጋይነት ከአሜሪካ ጋር ስለሚደረግ ንግግር ለመወያየት ኢስታምቡል ይገኛሉ።

  10. የአሜሪካ ምክር ቤት አባል በኢትዮጵያ ግጭት መቀስቀሱ እንዳሳሰባቸው ገለጹ

    ግሪጎሪ ሚክስ

    የፎቶው ባለመብት, Gregory Meeks/FB

    በአሜሪካ ምክር ቤት የውጭ ጉዳይ ኮሚቴ አባል የሆኑት ግሪጎሪ ሚክስ በሰሜን ኢትዮጵያ ግጭት መቀስቀሱ የሚሊዮኖችን ሕይወት ለአደጋ የሚያጋልጥ እና የቀጣናውን ሰላም የሚያናጋ ነው ሲሉ ስጋታቸውን ገለጹ።

    የኮንግረስ አባሉ ሚክስ ግጭቱን በተመለከተ ባወጡት መግለጫ ሁኔታው ኢትዮጵያን ወደ እርስ በርስ ጦርነት የሚመልስ እና “የትኛውም ወገን አትራፊ እንደማይሆን በመግለጽ ሰላማዊ መፍትሄ እንዲፈለግ ጠይቀዋል።

    ሚክስ “በግንቦት ተአማኒ ምርጫ ለማካሄድ ሁሉም ወገኖች ከግጭት ተቆጥበው እርዳታ ለሚያስፈልጋቸው እርዳታ የሚቀርብበትን መንገድ እንዲያመቻቹ፣ “የፕሪቶሪያው ስምምነት ሙሉ ለሙሉ ተግባራዊ መሆን አለበት” ብለዋል።

    “ኢትዮጵያን የገጠሟት ፖለቲካዊ ችግሮች በጦር ሜዳ ሊፈቱ አይችሉም። ለኢትዮጵያ ሕዝብ የተሻለ የወደፊት ዕጣ ፈንታ ለማስገኘት ዲፕሎማሲ፣ ነጻ እና ፍትሐዊ ምርጫ ብቸኞቹ አስተማማኝ መንገዶች ናቸው” በማለትም መክረዋል።

    ጠበቃ እና የዲሞክራቲክ ፓርቲ አባል የሆኑት ግሪጎሪ ጆርጅ ዋልደን ሚክስ ከኒው ዮርክ ተመርጠው የአሜሪካ ምክር ቤት አባል ሲሆኑ፣ በምክር ቤቱ የውጭ ጉዳይ ኮሚቴ ሊቀመንበር ሆነው ሰርተዋል። አሁንም የኮሚቴው አባል ናቸው።

  11. በኢራን የጅምላ እስር እየተካሄደ መሆኑ ተዘገበ

    ኢራን

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    በኢራን ለሳምንታት የተካሄደው ተቃውሞ ጋብ ካለ በኋላ ተጨማሪ ተቃውሞዎችን ለማስቆም ሲቪል የለበሱ የፀጥታ ኃይሎች የጅምላ እስር እና አፈሳ እያካሄዱ መሆናቸው ተነገረ።

    በአገሪቱ የተከሰተውን የኢኮኖሚ ቀውስ ሰበብ አድርጎ የተቀሰቀሰው ሕዝባዊ ተቃውሞ በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች ተስፋፍቶ ለሦስት ሳምንታት በተካሄደበት ጊዜ በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች መገደላቸው እና በአስር ሺዎች መታሰራቸው ተዘግቧል።

    የሥርዓት ለውጥ ወደ መጠየቅ የተስፋፋውን ተቃውሞ ተከትሎ ባለሥልጣናት የኢንተርኔት አገልግሎትን በማቋረጥ በእስራኤል እና በአሜሪካ የሚደገፉ ናቸው ያሏቸውን ተቃዋሚዎች ለመቆጣጠር ጭካኔ የተሞላበት ኃይል መጠቀማቸውን የሰብአዊ መብት ቡድኖች ከስሰዋል።

    ሮይተርስ አምስት ኢራናውያንን ጠቅሶ እንደዘገበው ሲቪል የለበሱ የኢራን መንግሥት የፀጥታ ኃይሎች መጠነ ሰፊ አፈሳ እያካሄዱ ሲሆን በመንገዶች እና በኬላዎች ላይ በርካታ የፀጥታ ኃይሎች በብዛት ይታያሉ።

    በቁጥጥር ሥር የሚውሉ ሰዎችም በምሥጢራዊ ቦታዎች እንደሚታሰሩ ኢራናውያኑ ለዜና ወኪሉ ተናግረዋል።

    አንድ ኢራናዊ "መንገድ ላይ ያገኙትን በሙሉ እየያዙ ነው።ወደ የት እንደሚወሰዱ እና የት እንደሚታሰሩ ማንም አያውቅም።በዚህም በሕዝቡ ውስጥ ፍርሃት ለመንዛት እየሞከሩ ነው” ብለዋል።

  12. የአውሮፓ ኅብረት የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብን በአሸባሪነት ፈረጀ

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    ኢራን ባለፉት ሳምንታት ተቃዋሚዎች ላይ የወሰደችውን በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎችን የገደለ እርምጃ ተከትሎ የአውሮፓ ኅብረት የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብን የአሸባሪዎች ዝርዝር ውስጥ አካተተ።

    የአውሮፓ ኅብረት ኮሚሽን ምክትል ፕሬዝዳንት የሆኑት ካጃ ካላስ፤ ይህ እርምጃ ኢራን ውስጥ ዋነኛ ወታደራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ፖለቲካዊ ኃይል የሆነውን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ እንደ አል ቃኢዳ እና ኢስላሚክ ስቴት ያሉ ጂሃዳዊ ቡድኖች ተርታ እንደሚያስቀምጠው ተናግረዋል።

    በአዲሱ ውሳኔ መሠረት የአውሮፓ ኅብረት በስድስት የኢራን ተቋማት እና በአገሪቱ በሚገኙ 15 ሰዎች ላይ ማዕቀብ ተጥሏል። ማዕቀብ ከተጣለባቸው መካከል የአገር ውስጥ ጉዳዮች ሚኒስትሩ እስካንዳር ሞሜኒ፣ ጠቅላይ ዐቃቤ ሕጉ ሞሐመድ ሞቫሄዲ አዛድ እንዲሁም ዋና ዳኛው ኢማን አፍሻሪ ይገኙበታል።

    የአውሮፓ ኅብረት የአሸባሪዎች ዝርዝር ውስጥ የተካተቱ ተቋማት የጉዞ እና የሀብት እገዳን ጨምሮ የተለያዩ ማዕቀቦች ያጋጥሟቸዋል። እነዚህ እርምጃዎች ማዕቀቡ የሚጣልባቸው አካላት ያላቸውን የድጋፍ መረብ ለመበጠስ ያለመ ነው።

    ኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ በበኩላቸው የአውሮፓ ኅብረት ውሳኔን "ተውኔታዊ" እና "ጉልህ ስትራቴጂክ ስህተት" ሲሉ ጠርተውታል።

    እጅግ ኃያል የኢራን ወታደራዊ ኃይል ስለሆነው እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ለማንበብ ይህንን ሊንክ ይጫኑ፦ ኢራን የምትተማመንበት እስላማዊው አብዮታዊ ዘብ ማን ነው? ምንስ አቅም አለው?

  13. አሜሪካ የኢራን ባለሥልጣናት እና ቤተሰቦቻቸው በአሜሪካ ያላቸውን መብት ገፈፈች

    የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማርኮ ሩቢዮ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የምስሉ መግለጫ, የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማርኮ ሩቢዮ

    የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የኢራን መንግሥት ከፍተኛ ባለሥልጣናት እና ቤተሰቦቻቸው አሜሪካ ውስጥ በመሆን የሚያገኙት መብት እና ጥቅም እንዲነሳ ማድረጉን አሳወቀ።

    የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤቱ እንደገለጸው በሚኒስትሩ በማርኮ ሩቢዮ ውሳኔ መሠረት የኢራን መንግሥት ከፍተኛ ባለሥልጣናት እና የቤተሰብ አባሎቻቸው አሜሪካንን የመጎብኘት እና ሌሎች መብቶች እንዳይኖሯቸው ተደርጓል።

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ በኤክስ ገጹ ላይ ባሰፈረው አጭር መልዕክት "የኢራን መንግሥት ከሚፈጽመው አደገኛ ጭቆና የሚጠቀሙ [ግለሰቦች] በአሜሪካ የኢሚግሬሽን ሥርዓት ውስጥ ተጠቃሚ እንዲሆኑ አይፈቀድላቸው” ብሏል።

    በአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የቆንስላ ጉዳዮች ረዳት ሚኒስትር የሆኑት ሞራ ናምዳር “የኢራን እስላመዊ መንግሥት አባላት እና የቅርብ ዘመዶቻቸው” የአሜሪካንን የኢሚግሬሽን እና ቪዛ ሥርዓት “አላግባብ እንዲጠቀሙበት አንፈቅድም” ብለዋል።

    አክለውም "አሜሪካ ከጀግኖቹ የኢራን ዜጎች ጎን ትቆማለች። ስለዚህም መሠረታዊ መብታቸውን በሚጠይቁ ዜጎቻቸው ላይ ጭካኔ የተሞላበት ጭቆና የሚፈጽመው መንግሥት አባላት እና ቤተሰቦቻቸው የአሜሪካንን የቪዛ እና የኢሚግሬሽን ሥርዓትን እንዲጠቀሙበት አንፈቅድም።”

    ነገር ግን የአሜሪካ መንግሥት በኢራን ከፍተኛ ባለሥልጣናት እና በቤተሰቦቻቸው ላይ የሚወሰደው የኢሚግሬሽን እርምጃ የቪዛ ስረዛ ብቻ ይሁን ወይም ቋሚ የመኖሪያ መብትን እና ዜግነትን እስከ መግፈፍ የሚደርስ ስለመሆኑ ያለው ነገር የለም።

  14. የቡርኪና ፋሶ ወታደራዊ መንግሥት ሁሉም የፖለቲካ ፓርቲዎች እንዲበተኑ ወሰነ

    ካፕቴይን ኢብራሒም ትራኦሬ ደጋፊዎች በተሰበሰቡበት በጠባቂዎቻቸው ተከበው

    የፎቶው ባለመብት, Ibrahim Traoré/X

    የምስሉ መግለጫ, ወጣቱ የቡርኪና ፋሶ ወታደራዊ መሪ ወደ ሥልጣን የመጡት በአውሮፓውያኑ 2022 የተደረገውን መፈንቅለ መንግሥት ተከትሎ ነው

    የቡርኪና ፋሶ ወታደራዊ መንግሥት ሁሉም ፖለቲካዊ ፓርቲዎች እንዲበተኑ እና የሚተዳደሩበት ሕጋዊ ማዕቀፍ እንዲፈርስ ወሰነ።

    ሐሙስ ዕለት ውሳኔውን ያስተላለፈው የምዕራብ አፍሪካዊቷ ሀገር የሚኒስትሮች ምክር ቤት መሆኑን ሮይተርስ የዜና ወኪል ዘግቧል።

    በአውሮፓውያኑ መስከረም 2022 በመፈንቅለ መንግሥት ወደ ሥልጣን የመጣው የካፕቴይን ኢብራሒም ትራኦሬ አገዛዝ ሥልጣኑን ለማራዘም የተለያዩ መንገዶች እየተጠቀመ ነው የሚል ትችት ይቀርብበታል።

    የቡርኪና ፋሶ የሀገር ውስጥ ሚኒስትር ኤሚል ዜርቦ ውሳኔው "ለሀገር መልሶ ግንባታ" የተላለፈ ነው በማለት ከዚህ ቀደም የነበረው መድብለ-ፓርቲ ሥርዓት ለብዝበዛ እና ለአሠራር ብልሹነት የተጋለጠ ነው ሲሉ መተቸታቸው ተሰምቷል።

    ሚኒስትሩ አክለው በሀገሪቱ የተለያዩ የፖለቲካ ፓርቲዎች መኖራቸው ለክፍፍል እና የማኅበረሰብ ጥምረት እንዲዳከም ምክንያት ሆኗል ብለዋል።

    ቡርኪና ፋሶ ከመፈንቅለ-መንግሥቱ በፊት ከ100 በላይ የተመዘገቡ የፖለቲካ ፓርቲዎች የነበሯት ሲሆኑ 15 ፓርቲዎች በአውሮፓውያኑ 2020 ከተደረገው ምርጫ በኋላ ወደ ፓርላማ መግባት ችለው ነበር።

    አዲሱ የመንግሥት ውሳኔ ሁሉም ፖለቲካዊ ፓርቲዎች እንዲፈርሱ ከማስገደዱም በተጨማሪ የተበተኑት ፓርቲዎች ንብረቶች ለመንግሥት ተላልፈው ይሰጣሉ።

    የሳሕል ቀጣናዋ ሀገር እንደ ጎረቤቶቿ ማሊ እና ኒጀር ከአል ቃኢዳ ጋር ግንኙነት ያለውን ኢስላሚክ ስቴት ታጣቂ ቡድን ለማዳከም እየጣረች ትገኛለች። ታጣቂ ቡድኑ በአካባቢው በርካታ ሰዎችን ገድሏል፤ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ሰዎች እንዲፈናቀሉም ምክንያት ሆኗል።

  15. የጦር መርከቦችን ወደ ኢራን የላኩት ትራምፕ “መጠቀም ባይኖርብን በጣም ጥሩ ይሆናል” አሉ

    የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ እና የአገሪቱ መከላከያ ሚኒስትር ፒት ሄግሴት

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ተጨማሪ የጦር መርከብ ወደ መካከለኛው ምስራቅ የላኩት የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ፤ ከኢራን ጋር ንግግር የማድረግ እቅድ እንዳላቸው ተናገሩ። የአገሪቱ መከላከያ ሚኒስትር ፒት ሄግሴት በበኩላቸው ሠራዊቱ ፕሬዝዳንቱ ውሳኔ በሚያሳልፉበት ወቅት እርምጃ ለመውሰድ ዝግጁ መሆኑን ገልጸዋል።

    ትራምፕ ኢራን ላይ ለማድረግ ስላቀዱት ንግግር ይዘት፣ መቼ ሊካሄድ እንደሚችል አልያም ዋሺንግተን ድርድሩን ትመራው እንደሆነ ከመናገር ተቆጥበዋል።

    ትራምፕ ከቴህራን ጋር ሊደረግ ስለሚችል ድርድር ከጋዜጠኞች ለቀረበላቸው ጥያቄ “እያቀድኩበት ነው” የሚል ምላሽ ሰጥተዋል። “በአሁኑ ሰዓት በጣም ግዙፍ፣ በጣም ኃይለኛ የሆኑ መርከቦቻችን ወደ ኢራን እየቀዘፉ ነው። እነርሱን መጠቀም ባይኖርብን በጣም ጥሩ ይሆናል” ማለታቸውን የዜና ወኪሉ ሮይተርስ ዘግቧል።

    ትራምፕ፤ ኢራንን ማጥቃትን በተመለከተ አማራጮቻቸውን እያዩ ቢሆንም ውሳኔ ላይ እንዳልደረሱ የአሜሪካ ባለስልጣናት ተናግረዋል። የአሜሪካ እና ኢራን ውጥረት ከቅርብ ሳምንታት ወዲህ እንደገና ያገረሸው የቴህራን እስላማዊ መንግሥት በተቃዋሚዎች ላይ የወሰደውን እርምጃ ተከትሎ ነው።

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት፤ ኢራን ተቃዋሚዎችን መግደሏን የምትቀጥል ከሆነ እርምጃ እንደሚወስዱ ሲዝቱ ቆይተዋል። በኢኮኖሚ መላሸቅ እና ፖለቲካዊ አፈና ምክንያት በመላው አገሪቱ የተነሳው ተቃውሞ ባለፉት ቀናት ረግቧል።

    የእስራኤል እና የአሜሪካ ኃይሎች ሰኔ ውስጥ በዋና ዋና የኒውክሌር ተቋማቷ ላይ የአየር ጥቃት የፈጸሙባት ኢራን፤ በድጋሚ የኒውክሌር ፕሮግራሟን እንደገና የምታስቀጥል ከሆነ ዋሺንግተን እርምጃ እንደምትወስድ ትራምፕ አስጠንቅቀዋል።

    ለሰሞኑ ደግሞ ከፍተኛ የአሜሪካ ጦር በቀጣናው ተሰባስቧል። የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር ሄግሴት የኢራን ሁኔታን በተመለከተ አስተያየት እንዲሰጡ በትራምፕ ጥያቄ ቀርቦላቸው ነበር።

    የትራምፕ አስተዳደር የመከላከያ ሚኒስቴርን ስያሜ ይፋዊ ባልሆነ መንገድ "የጦርነት ሚኒስቴር" ብሎ መቀየሩን ያስታወቁት ሄግሴት፤ "የኒውክሌር አቅም ሊኖራቸው አይገባም። ፕሬዝዳንቱ ከጦርነት ሚኒስቴሩ የሚጠብቁትን ማንኛውንም ነገር ለማቅረብ ዝግጁ ነን" ብለዋል።

  16. የአሜሪካ ባለሥልጣናት በኢራን ጉዳይ ከእስራኤል እና ሳዑዲ ጋር ሊመክሩ ነው

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ እና ልዑል ሰልማን

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ፕሬዝዳንት ትራምፕ እና ልዑል ሰልማን

    ሁለት ከፍተኛ የአሜሪካ ባለሥልጣናት የኢራንን ጉዳይ በተመለከተ ከእስራኤል እና ከሳዑዲ አረቢያ የመከላከያ እና ደኅንነት ባለሥልጣናት ጋር ሊመካከሩ እንደሆነ የአሜሪካው አክሲዮስ ዘገበ።

    የአሜሪካ የጦር መርከቦች ወደ መካከለኛው ምሥራቅ መቃረባቸውን ተከትሎ አሜሪካ በኢራን ላይ ጥቃት ልትፈጽም ትችላለች በሚል ተሰግቷል።

    የፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አስተዳደር ተጨማሪ የጦር መርከብ ወደ ሥፍራው መላኩም ተዘግቧል።

    ላለፉት ቀናት እስራኤል፣ ሳዑዲ አረቢያ እና ሌሎችም የቀጣናው አገራት አሜሪካ በኢራን ላይ ጥቃት ትሰነዝራለች በሚል ስጋት ውስጥ ናቸው።

    በኢራን ውስጥ ያሉ ዒላማዎችን በተመለከተ እስራኤል እና አሜሪካ መረጃ እየተለዋወጡ እንደሆነ የአሜሪካው መገናኛ ብዙኃን አክሲዮስ በድረ ገጹ ያወጣው መረጃ ይጠቁማል።

    ጦርነት ሊነሳ ይችላል የሚል ስጋት ውስጥ የወደቀችው ሳዑዲ አረቢያም ዲፕሎማሲያዊ መፍትሔ እየፈለገች ትገኛለች።

    የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ኃላፊ ማርኮ ሩቢዮ ከዚህ ቀደም በኮንግረስ ኮሚቴ ባደረጉት ንግግር የኢራን መንግሥት “ከመቼውም ጊዜ በላይ አሁን ተዳክሟል። ውድቀት ይጠብቀዋል” ብለዋል።

    ሕዝባዊ ተቃውሞ በበረታበት ኢራን ጠቅላይ መሪው አሊ ኻሜኒ ከሥልጣን ቢወገዱ በማን እንደሚተኩ እንደማይታወቅም ተናግረዋል።

    የኢራን ጉዳይ ከቬንዝዌላ በላይ ውስብስብ እንደሆነ የገለጹት ማርኮ ሩቢዮ፤ “ጥንቃቄ የሚሻ ነገር ነው” ብለዋል።

    አሜሪካ በቀጣናው ያሉ ዜጎቿን ለመጠበቅ ስትል “ጊዜውን ያልጠበቀ ጥቃት ልትፈጽም እንደምትችል” ቢናገሩም፤ ትራምፕ ግን ውሳኔ ላይ አለመድረሳቸውን ገልጸዋል።

  17. ተጨማሪ የአሜሪካ ጦር መርከብ ወደ ባሕረ ሰላጤው ደረሰ

    ዩኤስኤስ ዴልበርት ዲ ብላክ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ዩኤስኤስ ዴልበርት ዲ ብላክ

    የአሜሪካ የጦር መርከቦች ቡድን ወደ መካከለኛው ምሥራቅ መሰማራታቸውን ተከትሎ አሜሪካ በኢራን ላይ ጥቃት ትፈጽማለች የሚል ስጋት በበረታበት በአሁኑ ወቅት ተጨማሪ የጦር መርከብ ወደ ሥፍራው ደርሷል።

    ዘመናዊው የጦር አውሮፕላን እና መርከቦችን እንዲሁም ሚሳዔሎችን ማውደም የሚችለው ዩኤስኤስ ዴልበርት ዲ ብላክ የተባለው በሱዩዝ ካናል በኩል በማቋረጥ ወደ ባሕረ ሰላጤው አካባቢ ሲያመራ ረቡዕ መታየቱን የባሕር ላይ እንቅስቃሴን የሚከታተለው ‘ማሪን ትራፊክ’ የተባለው ድረ ገጽ አመልክቷል።

    ግዙፉ የጦር አውሮፕላኖች ተሸካሚ መርከብ አብርሃም ሊንከንን ጨምሮ በአሁኑ ጊዜ ቢያንስ 10 የአሜሪካ የጦር መርከቦች በመካከለኛው ምሥራቅ አካባቢ እንደሚገኙ ይታመናል።

    ማክሰኞ ዕለት አንድ የአሜሪካ ባለሥልጣን ግዙፉ መርከብ ወደ አካባቢው እንደደረሰ ለቢቢሲ ቢያረጋግጡም በመርከቦች እንቅስቃሴ መከታተያ ላይ ግን ከሳምንት በላይ ሳይታይ ቆይቷል።

    የቢቢሲ መረጃ ማጣሪያ (ቢቢሲ ቬሪፋይ) ዛሬ ጠዋት እንዳረጋገጠው ኦስፕሬይ የተባሉት ወደ ተለያዩ አቅጣጫዎች በቀላሉ መብረር የሚችሉት የአሜሪካ ባሕር ኃይል ወታደራዊ አውሮፕላኖች በባሕረ ሰላጤው አካባቢ ወደ ኦማን ሲበር ተመልክቷል። ይህም ግዙፉ አውሮፕላን ተሸካሚ መርከብ ወደ አካባቢው መድረሱን የሚያመለክት ነው።

    በተጨማሪም አቡ ዳቢ ውስጥ ከሚገኘው ጦር ሰፈር የተነሳ የአሜሪካ ባሕር ኃይል ቃኚ ድሮን በኢራን የባሕር ዳርቻ አቅራቢያ ቅኝት እያደረጉ መሆኑ ተዘግቧል።

    ቢቢሲ ቬሪፋይ ከሳተላይት ምሥሎች እንዳጣራው ኢራን ከዳርቻዋ ጋር በሚዋሰነው ሆርሙዝ ሰርጥ ድሮን ተሸመሚ መርከቧን አሰማርታለች። መርከቧ የአየር ጥቃት መከከላያ ሥርዓት ያለት ሲሆን፣ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸውን ድሮኖች እና ሄሊኮፕተሮችን የምትይዝ ናት።

  18. ኢራን ለተባበሩት መንግሥታት ዋና ፀሐፊ ደብዳቤ ጻፈች

    የኢራን ወታደር ለአገሪቱ መሪ ምሥል ሰላምታ ሲሰጥ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ኢራን ወደ ድርድር የማትመጣ ከሆነ አሜሪካ እርምጃ የምትወስድበት ጊዜ መቃረቡን ፕሬዝዳንት ትራምፕ በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ ማስጠንቀቃቸውን ተከትሎ ኢራን ለተባበሩት መንግሥታት የአቤቱታ ደብዳቤ አቀረበች።

    በተባበሩት መንግሥታት አምባሳደር እና ቋሚ መልዕክተኛዋ አሚር ሳኢድ በኩል የኢራን ለድርጅቱ ዋና ፀሐፊ ባስገባቸው ደብዳቤ ዛቻው የመንግሥታቱ ድርጅትን “ቻርተር በግልጽ የሚጥስ” በመሆኑ የፀጥታው ምክር ቤት በማውገዝ ምላሽ እንዲሰጥ ጠይቀዋል።

    የትራምፕ መልዕክት “የኃይል እርምጃ ለመውሰድ ግልጽ እና የማያሻማ” ዛቻ በመሆኑ የዓለም አቀፍ ሕግን የሚቃረን እና የተባበሩት መንግሥታትን ቻርተር የሚጥስ ነው በማለት ድርጅቱ እርምጃ እንዲወስድ የኢራን አምባሳደር እና ቋሚ መልዕክተኛ ጠይቀዋል።

    ኢራን ለመንግሥታቱ ድርጅት በጻፈችው ደብዳቤ "እንዲህ ዓይነቱ ባህሪ ቀጣናዊ ውጥረትን የሚያባብስ፣ ያልታሰበባቸው ክስተቶች እንዲፈጠሩ የሚያደርግ እንዲሁም ለዓለም አቀፍ ሰላም እና ደኅንነት ቀጥተኛ አደጋ ነው” ብላለች።

    ደብዳቤው ጨምሮም "የትኛውም ዓይነት ጠብ አጫሪነት ወይም ወታደራዊ ጥቃት የሚፈጸም ከሆነ፣ ኢራን ሉዓላዊነቷን፣ የግዛት አንድነቷን እና ሕዝቧን ለመከላከል ሁሉንም አስፈላጊ እርምጃዎች ትወስዳለች” በማለት አስጠንቅቋል።

    ይህንንም ተከትሎ ለሚከሰት የትኛውም ዓይንት ከቁጥጥር ውጪ የሚሆን ቀውስ “ዩናይትድ ስቴትስ ሙሉ ተጠያቂ ትሆናለች” ስትል ኢራን እራሷን ለመከላከል እርምጃ እንደምትወስድ ለተባበሩት መንግሥታት በጻፈችው ደብዳቤ ገልጻለች።

  19. "አሜሪካ ሐቀኛ ከሆነች ለመደራደር ዝግጁ ነን" የኢራን አፈ-ጉባዔ

    የኢራኑ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራቅቺ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የኢራኑ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራቅቺ አርብ ወደ ቱርክ ያቀናሉ

    ኢራን ጥቃት ልትሰነዝርባት እየዛተች ካለችው አሜሪካ ጋር ሐቀኛ ድርድር ለማድረግ ፍላጎት እንዳላት አንድ ከፍተኛ ባለሥልጣኗ ተናገሩ።

    የኢራን ፓርላማ አፈ-ጉባዔ ሞሐመድ ባቀር ቃሊባፍ እንዳሉት "አሜሪካ ሐቀኛ ከሆነች ለመደራደር ዝግጁ ነኝ" ማለታቸው ተሰምቷል።

    አፈ-ጉባዔው ከሲኤንኤን ጋር በነበራቸው ቆይታ "ቴህራን ከዩናይትድ ስቴትስ ጋር ለመደራደር ዝግጁ ናት። ነገር ግን ይህ የሚሆነው ንግግሩ ሐቀኛ እና እውነተኛ ከሆነ ብቻ ነው" ብለዋል።

    አፈ-ጉባዔው ሀገራቸው ለድርድር ዝግጁ መሆኗን ቢጠቅሱም የአሜሪካው ፕሬዝደንት ግን "ፈቃዳቸውን ለማስፈፀም" እንጂ ለሐቀኛ ወይይት ዝግጁ አይደሉም ሲሉ ወቅሰዋል።

    ሞሐመድ በቅርቡ በኢራን ለተከሰተው ሕዝባዊ ተቃውሞ "የውጭ ኃይሎች" ያሏቸውን አካላት ተጠያቂ አድርገዋል።

    ባለሥልጣኑ በተቃውሞው የሞቱ ሰዎችን ቁጥር ይፋ ባያደርጉም በአመፁ ምክንያት "የተሰዉ 300 የፀጥታ አባላትን ደም" መንግሥታቸው "እንደሚበቀል" ተናግረዋል።

    የሰብአዊ መብት ተቆርቋሪዎች እንደሚሉት ለሦስት ሳምንታት ያህል በቆየው ተቃውሞ ከስድስት ሺህ በላይ ሰዎች በኢራን መንግሥት የፀጥታ ኃይሎች ተገድለዋል።

    በተያያዘ ዜና የኢራኑ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራቅቺ ከአሜሪካ ጋር ስላለው ውጥረት ለማውራት አርብ ወደ ቱርክ እንደሚያቀኑ ሮይተርስ የዜና ወኪል ዘግቧል።

    የአሜሪካው ፕሬዝደንት ረቡዕ ባስተላለፉት መልዕክት ኢራን የኒውክሌር ስምምነት እንድትፈፅም አስጠንቅቀው ይህ ካልሆነ ቴህራን ላይ ከባድ ቅጣት እንደሚጥሉ ዝተዋል።

    ትራምፕ ግዙፉን ዩኤስኤስ አብርሀም ሊንከንን ጨምሮ የተለያዩ የጦር መርከቦችን ወደ መካከለኛው ምሥራቅ መላካቸውን ተነግሯል።

    ከጥቂት ሳምንታት በፊት ከኢራን አብዮት በኋላ ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ ለተቀሰቀሰው ሕዝባዊ አመፅ የአሊ ኻሜኒ መንግሥት እስራኤል እና ዩናይትድ ስቴትስን ተጠያቂ ያደርጋል።

  20. ካፍ የሴኔጋል አሠልጣኝ እና ተጫዋቾች ላይ ቅጣት አስተላለፈ

    አሰልጣን ፓፔ ቲያው

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የአፍሪካ እግር ኳስ ፌዴሬሽኖች ማኅበር (ካፍ) የሴኔጋሉ አሠልጣኝ ፓፔ ቲያው ለአምስት ጨዋታዎች ከሜዳ እንዲርቁ ቅጣት አስተላልፏል።

    በተጨማሪም አሠልጣኙ “ስፖርታዊ ጨዋነት የጎደለው ተግባር” በመፈፀማቸው 100 ሺህ ዶላር እንዲከፍሉ ታዘዋል።

    ቲያው ሞሮኮ ባዘጋጀችው የአፍሪካ ዋንጫ ፍፃሜ ላይ የመሐል ዳኛውን ውሳኔ በመቃወም ተጫዋቾቹ ሜዳ ለቀው እንዲወጡ ሲያበረታቱ ታይተዋል።

    ካፍ ከአሠልጣኙ በተጨማሪ የሴኔጋል እግር ኳስ ፌዴሬሽን ላይ የ615 ሺህ ዶላር ቅጣት አስተላልፏል።

    የሴኔጋል ተጫዋቾች የሆኑት ኢሊማን ንዲያዬ እና ኢስማይላ ሳር ዳኛው ላይ ባሳዩት ያልተገባ ባህሪ ለሁለት ጨዋታዎች እንዳይሰለፉ ተቀጥተዋል።

    ሞሮኮ የሴኔጋል ተጫዋቾች በፍፃሜው ጨዋታ ከሜዳ ለቀው በመውጣታቸው ውጤቱ ሊቀለበስ ይገባል በሚል ያስገባችውን ጥያቄ የካፍ የዲሲፕሊን ኮሚቲ ውድቅ አድርጎታል።

    ካፍ ሞሮኮ ላይም ቅጣት ያስተላለፈ ሲሆን፣ የዋንጫው አዘጋጅ ሀገር 315 ሺህ ዶላር እንድትከፍል ታዛለች።

    ካፍ ሞሮኮ ላይ ቅጣት የጣለው የኳስ አቀባይ ታዳጊዎች ያልተገባ ተግባር በማሳየታቸው፣ የተጫዋቾች እና አሠልጣኞች ባህሪ እንዲሁም ደጋፊዎች የሚያብለጨለጭ ጨረር በመልቀቃቸው ነው።

    አምበሉ አሽራፍ ሐኪሚ ሁለት ጨዋታዎች፣ ሌላኛው የሞሮኮ ተጫዋች ሳይባሪ ደግሞ የሴኔጋሉ በረኛ ኤድዋርድ ሜንዲን ፎጣ ለመውሰድ በመሞከር ሦስት ጨዋታዎች ተቀጥተዋል።

    በጭማሪ ደቂቃ ሴኔጋል ያስቆጠረችውን ግብ ዳኛው መሻራቸው፤ ከጥቂት ደቂቃ በኋላ ደግሞ ለሞሮኮ ፍፁም ቅጣት ምት መስጠታቸውን ተከትሎ ፓፔ ቲያው ተጫዋቾቻቸው ከሜዳ እንዲወጡ አድርገው ነበረ።

    ጨዋታው ከ17 ደቂቃ መቋረጥ በኋላ የቀጠለ ሲሆን፣ ፓፔ ጌዬ ባስቆጠራት ግል ሴኔጋል የአፍሪካ ዋንጫ ባለቤት መሆን ችላለች።